ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ኢሳይያስ 63:8-18 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

8. እርሱም፣ “ርግጥ ነው፤ እነርሱ ሕዝቤ ናቸው፤የማይዋሹኝ ወንዶች ልጆቼ ናቸው” አለ።ስለዚህም አዳኝ ሆነላቸው።

9. በጭንቃቸው ሁሉ ተጨነቀ፤የፊቱም መልአክ አዳናቸው፤በፍቅሩና በምሕረቱ ዋጃቸው፤በቀደመው ዘመን ሁሉ አነሣቸው፤ተሸከማቸውም።

10. እነርሱ ግን ዐመፁ፤ቅዱስ መንፈሱንም አሳዘኑ፤ስለዚህ ተመልሶ ጠላት ሆናቸው፤እርሱ ራሱ ተዋጋቸው።

11. ከዚያም ሕዝቡ የጥንቱን ዘመን፣የሙሴንና የሕዝቡን ጊዜ እንዲህ በማለት አስታወሱ፤የበጎቹን እረኛ፣ከባሕሩ ያወጣቸው እርሱ የት አለ?ቅዱስ መንፈሱንም፣በመካከላቸው ያኖረ እርሱ የት አለ?

12. የከበረው ኀያል ክንድ፣በሙሴ ቀኝ እጅ ላይ እንዲያርፍ አደረገ፤ለራሱ የዘላለም ዝና እንዲሆንለት፣ውሆችን በፊታቸው ከፈለ።

13. ፈረስ በምድረ በዳ እንደሚያልፍ ሁሉ፣እነርሱንም በጥልቁ ውስጥ አሳልፎ መራቸው፤ስለዚህም አልተሰናከሉም፤

14. ወደ ሸለቆ እንደሚወርድ የከብት መንጋ፣ በእግዚአብሔር መንፈስ ዕረፍት ተሰጣቸው።ሕዝብህን በዚህ ሁኔታ የመራሃቸው፣ስምህን የከበረ ለማድረግ ነው።

15. ከተቀደሰው፣ ከተከበረውና ከፍ ካለው ዙፋንህ፣ከሰማይ ወደ ታች ተመልከት፤ኀይልህና ቅናትህ የት አለ?ገርነትህና ርኅራኄህ ከእኛ ርቀዋል።

16. አብርሃም ባያውቀን፣እስራኤልም ባያስታውሰን እንኳ፣አንተ እኮ አባታችን ነህ፤ እግዚአብሔር ሆይ፤ አንተ አባታችን ነህ፤ከጥንትም ቢሆን ስምህ “ቤዛችን” ነው።

17. እግዚአብሔር ሆይ፤ ከመንገድህ እንድንወጣ፣ልባችንን በማደንደን ለምን እንዳንፈራህ አደረግኸን?ስለ ባሮችህ ስትል፣ስለ ርስትህ ነገዶች ስትል እባክህ ተመለስ።

18. ለጥቂት ጊዜ ሕዝብህ የተቀደሰውን ስፍራ ወርሶ ነበር፤አሁን ግን ጠላቶቻችን መቅደስህን ረገጡት።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ኢሳይያስ 63