ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ኢሳይያስ 47:5-15 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

5. “አንቺ የባቢሎናውያን ልጅ ሆይ፤ወደ ጨለማ ግቢ፤ ዝም ብለሽም ተቀመጪ፤ከእንግዲህ የመንግሥታት እመቤት፣ተብለሽ አትጠሪም።

6. ሕዝቤን ተቈጥቼ ነበር፤ርስቴን አርክሼው ነበር፤አሳልፌ በእጅሽ ሰጠኋቸው፤አንቺ ግን አልራራሽላቸውም፤በዕድሜ በገፉት ላይ እንኳ፣እጅግ ከባድ ቀንበር ጫንሽባቸው።

7. አንቺም፣ ‘እስከ መጨረሻው፣ለዘላለም ንግሥት እሆናለሁ!’ አልሽ፤ሆኖም እነዚህን ነገሮች አላስተዋልሽም፤ፍጻሜያቸው ምን እንደሚሆንም አላሰብሽም።

8. “አሁንም አንቺ ቅምጥል ፍጡር፣በራስሽ ተማምነሽ የምትቀመጪ፣በልብሽም፣‘እኔ ነኝ፣ ከእኔ በቀር ሌላ የለም፤ከእንግዲህ መበለት አልሆንም፤የወላድ መካንም አልሆንም’ የምትይ ስሚ!

9. እነዚህ ሁለት ነገሮች፣መበለትነትና የወላድ መካንነት፣አንድ ቀን ድንገት ይመጡብሻል፤የቱን ያህል አስማት፣የቱንም ያህል መተት ቢኖርሽ፣በሙሉ ኀይላቸው ይመጡብሻል።

10. በክፋትሽ ተማምነሽ፣‘ማንም አያየኝም’ አልሽ፤ደግሞም፣ ‘እኔ ነኝ፣ ከእኔ በቀር ሌላ የለም’ባልሽ ጊዜ፣ጥበብሽና ዕውቀትሽ አሳሳቱሽ።

11. ጥፋት ይመጣብሻል፤ነገር ግን በአስማትሽ እንዴት እንደም ታርቂው አታውቂም፤ወጆ ከፍለሽ ለማስወገድ የማትችዪው፣ጒዳት ይወድቅብሻል፤ያላሰብሽው አደጋ፣ድንገት ይደርስብሻል።

12. በይ እንግዲህ፣ “ከልጅነትሽ ጀምሮ የደከምሽባቸውን፣አስማቶችሽን፣ብዙ መተቶችን ቀጥዪባቸው፤ምናልባት ይሳካልሽ፤ምናልባትም ጠላቶችሽን ታሸብሪባቸው ይሆናል።

13. የተቀበልሽው ምክር ሁሉ ድካም ብቻ ሆኖ አስቀርቶሻል፤እነዚያ ከወር እስከ ወር ከዋክብትን አንጋጦ በማየት የሚተነብዩ፣ኮከብ ቈጣሪዎች እስቲ ይምጡ፤ከሚደርስብሽም ነገር እስቲ ያድኑሽ።

14. እነሆ፣ እነርሱ ገለባ ናቸው፤እሳት ይበላቸዋል፤ከነበልባሉ ወላፈን የተነሣ፣ራሳቸውን ማዳን አይችሉም።ሰው የሚሞቀው ፍም አይኖርም፤ተቀምጠው የሚሞቁትም እሳት የለም።

15. ከልጅነት ጀምሮ አብረሻቸው የደከምሽው፣አብረሽ የተገበያየሻቸው፣ሊያደርጉ የሚችሉት ይህንኑ ብቻ ነው።እያንዳንዱ በስሕተቱ ይገፋበታል፤አንቺን ግን የሚያድን የለም።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ኢሳይያስ 47