ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ኢሳይያስ 33:10-24 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

10. እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ “አሁን እነሣለሁ፤አሁን ከፍ ከፍ እላለሁ፤አሁን እከብራለሁ።

11. ገለባን ፀነሳችሁ፤እብቅንም ወለዳችሁ፤እስትንፋሳችሁም የሚበላችሁ እሳት ነው።

12. ሕዝቦች ኖራ እንደሚወጣው ድንጋይ ይቃጠላሉ፤እንደ እሾኽ ቍጥቋጦ በእሳት ይጋያሉ።”

13. እናንት በሩቅ ያላችሁ ያደረግሁትን ስሙ፤እናንት በቅርብ ያላችሁ ኀይሌን ዕወቁ!

14. በጽዮን ያሉ ኀጢአተኞች ደነገጡ፤አምላክ የሌላቸውም ፍርሀት ይዞአቸው፣“ከእኛ መካከል ከሚባላ እሳት ጋር ማን መኖር ይችላል፣ከዘላለም እሳትስ ጋር ማን መኖር ይችላል?” አሉ።

15. በጽድቅ የሚራመድ፣ቅን ነገር የሚናገር፣በሽንገላ የሚገኝ ትርፍ የሚንቅ፣መማለጃን ላለመቀበል እጁን የሚሰበሰብ፣የግድያን ሤራ ላለመስማት ጆሮውን የሚደፍን፣ክፋትን ላለማየት ዐይኑን የሚጨፍን፣

16. ይህ ሰው በከፍታ ላይ ይኖራል፤የተራራም ምሽግ መጠጊያው ይሆናል፤እንጀራ ይሰጠዋል፣ውሃውም አይቋረጥበትም።

17. ዐይኖችህ ንጉሡን በውበቱ ያዩታል፤በሩቅ የተዘረጋችውንም ምድር ይመለከታሉ።

18. የቀደመው መከራ ትዝ እያለህ፣“ያ ዋና አለቃ የት አለ?ግብር ተቀባዩስ ወዴት ሄደ?የመጠበቂያ ማማ ኀላፊውስ የት አለ?” ትላለህ።

19. እነዚያ ንግግራቸው የማይገባ፣የሚሉትም የማይታወቅ፣ሊረዱት የማይቻል ቋንቋ የሚናገሩትን ጋጠወጥ ሕዝብ ከእንግዲህ አታያቸውም።

20. በዓላታችንን የምናከብርባትን ከተማ ጽዮንን ተመልከት፤ሰላማዊ መኖሪያ፣ የማትነቃነቅ ድንኳን የሆነችውን፣ካስማዋ የማይነቀል፣ከገመዷ አንዱ እንኳ የማይበጠሰውን፣ኢየሩሳሌምን ዐይኖችህ ያያሉ።

21. እግዚአብሔር በዚያ ኀይላችን ይሆናል፤ባለ መቅዘፊያ ጀልባዎች እንደማያል ፉባቸው፣ታላላቅ መርከቦችም እንደማይሻገሯቸው፣ሰፋፊ ወንዞችና ጅረቶች ይሆንልናል።

22. እግዚአብሔር ዳኛችን ነው፤ እግዚአብሔር ሕግ ሰጪያችን ነው፤ እግዚአብሔር ንጉሣችን ነው፤የሚያድነንም እርሱ ነውና።

23. መወጠሪያ ገመድህ ላልቶአል፤ምሰሶው ጠብቆ አልተተከለም፤ሸራው አልተወጠረም፤በዚያ ጊዜ ታላቅ ምርኮ ይከፋፈላል፤አንካሳ እንኳ ሳይቀር ምርኮ ይወስዳል።

24. በጽዮን ተቀምጦ፣ “ታምሜአለሁ” የሚል አይኖርም፤በዚያ የሚኖሩ ሰዎች ኀጢአትም ይቅር ይባላል።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ኢሳይያስ 33