ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ሰቆቃወ 3:1-15 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. በቊጣው በትር፣መከራ ያየ ሰው እኔ ነኝ።

2. ከፊቱ አስወጣኝ፤በብርሃን ሳይሆን በጨለማ እንድሄድ አደረገኝ።

3. በእርግጥ ቀኑን ሁሉ በመደጋገም፣እጁን በላዬ ላይ መለሰ።

4. እርሱ ሥጋዬንና ቈዳዬን አስረጀ፤ዐጥንቶቼንም ሰባበረ።

5. በምሬትና በድካም፣ቅጥር ሠራብኝ፤ ዙሪያዬንም ከበበኝ።

6. ከሞቱ ብዙ ጊዜ እንደሆናቸው፣በጨለማ እንድኖር አደረገኝ።

7. በቅጥር ውስጥ ዘጋብኝ፤ ስለዚህ ማምለጥ አልቻልሁም፤የእስር ሰንሰለቴንም አከበደብኝ።

8. ርዳታ ፈልጌ ብጣራና ብጮኽ እንኳ፣ጸሎቴን መስማት አልፈለገም።

9. መንገዴን በተጠረቡ ድንጋዮች ዘጋ፤ጐዳናዬንም አጣመመ።

10. አሸምቆ እንደ ተኛ ድብ፣እንደ አደባም አንበሳ፣

11. ከመንገድ ጐትቶ አስወጣኝ፤ ቈራረጠኝም፤ያለ ረዳትም ተወኝ።

12. ቀስቱን ገተረ፤ለፍላጻዎቹም ዒላማ አደረገኝ።

13. ፍላጻዎችን ከሰገባው አውጥቶ፣ልቤን ወጋው።

14. ለሕዝቤ ሁሉ ማላገጫ ሆንሁኝ፤ቀኑን ሙሉ በመሣለቅ ያዜሙብኛል።

15. መራራ ሥር አበላኝ፤ሐሞትም አጠገበኝ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ሰቆቃወ 3