ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ምሳሌ 30:17-32 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

17. “በአባት ላይ የምታፌዝ ዐይን፣የእናትንም ትእዛዝ የምትንቅ፣የሸለቆ ቊራዎች ይጐጠጒጧታል፤ጆፌ አሞሮችም ይበሏታል።

18. “እጅግ የሚያስደንቁኝ ሦስት ነገሮች አሉ፤የማላስተውላቸውም አራት ናቸው፤

19. የንስር መንገድ በሰማይ፣የእባብ መንገድ በቋጥኝ፣የመርከብ መንገድ በባሕር፣የሰውም መንገድ ከሴት ልጅ ጋር ናቸው።

20. “የአመንዝራዪቱ መንገድ ይህ ነው፤በልታ አፏን በማበስ፣‘ምንም የሠራሁት ጥፋት የለም’ ትላለች።

21. “ምድር በሦስት ነገር ትናወጣለች፤እንዲያውም መሸከም የማትችላቸው አራት ነገሮች ናቸው፤

22. ባሪያ ሲነግሥ፣ሰነፍ እንጀራ ሲጠግብ፣

23. የተጠላች ሴት ባል ስታገባ፣ሴት ባሪያ በእመቤቷ እግር ስትተካ።

24. “በምድር ላይ አራት ነገሮች ትንንሽ ናቸው፤ሆኖም እጅግ ጠቢባን ናቸው፤

25. ጒንዳኖች ደካማ ፍጡራን ናቸው፤ሆኖም ምግባቸውን በበጋ ያከማቻሉ።

26. ሽኮኮዎች ዐቅመ ደካማ ናቸው፤ሆኖም መኖሪያቸውን በቋጥኞች መካከል ይሠራሉ፤

27. አንበጦች ንጉሥ የላቸውም፤ሆኖም ቅደም ተከተል ይዘው ይጓዛሉ፤

28. እንሽላሊት በእጅ ትያዛለች፤ሆኖም በቤተ መንግሥት ትገኛለች።

29. “አረማመዳቸው ግርማዊ የሆነ ሦስት ነገሮች አሉ፤እንዲያውም በሞገስ የሚጐማለሉ አራት ናቸው፤

30. ከአራዊት መካከል ኀይለኛ የሆነው፣ከምንም ነገር ፊት ግንባሩን የማያጥፈው አንበሳ፤

31. ጐርደድ ጐርደድ የሚል አውራ ዶሮ፣ አውራ ፍየል፣እንዲሁም በሰራዊቱ የታጀበ ንጉሥ ናቸው።

32. ተላላ ሆነህ ራስህን ከፍ ከፍ ካደረግህ፣ወይም ክፉ ነገር ካቀድህ፣እጅህን በአፍህ ላይ አድርግ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ምሳሌ 30