ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ሕዝቅኤል 39:6-18 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

6. በማጎግና ያለ ሥጋት በባሕር ዳርቻ በሚኖሩት ላይ እሳት እሰዳለሁ፤ እነርሱም እኔ እግዚአብሔር እንደሆንሁ ያውቃሉ።”

7. “ ‘ቅዱሱ ስሜ በሕዝቤ በእስራኤል ዘንድ እንዲታወቅ አደርጋለሁ፤ ከእንግዲህ ወዲያ ቅዱስ ስሜ እንዲናቅ፣ እንዲቃለል አልፈልግም፤ አሕዛብም እኔ እግዚአብሔር የእስራኤል ቅዱስ እንደሆንሁ ያውቃሉ።

8. እነሆ ይመጣል፤ በእርግጥም ይሆናል፤ ይላል ጌታ እግዚአብሔር፤ ያ ያልሁት ቀን ይህ ነው።

9. “ ‘ከዚያም በእስራኤል ከተሞች የሚኖሩ ሁሉ ወጥተው የጦር መሣሪያውን፣ ትልልቁንና ትንንሹን ጋሻ፣ ቀስቱን፣ ፍላጻውን፣ የጦር ዱላውንና ጦሩን ሰብስበው ማገዶ በማድረግ ያነዱታል፤ ሰባት ዓመት ይማግዱታል።

10. ከሜዳ ላይ ዕንጨት መልቀም፣ ከዱርም ዛፍ መቍረጥ አያስፈልጋቸውም፤ የጦር መሣሪያቸውን በመማገድ ይጠቀማሉና። የዘረፏቸውን ይዘርፋሉ፤ የበዘበዟቸውን ይበዘብዛሉ፤ ይላል ጌታ እግዚአብሔር።

11. “ ‘በዚያ ቀን ሰዎች በምሥራቅ በኩል ወደ ባሕሩ በሚጓዙበት ሸለቆ፣ ለጎግ የመቃብር ስፍራ በእስራኤል እሰጠዋለሁ። ጎግና ሰራዊቱ ሁሉ በዚያ ስለሚቀበሩ፣ የተጓዦችን መንገድ ይዘጋሉ፤ ስለዚህም የሐሞን ጎግ ሸለቆ ይባላል።

12. “ ‘ምድሪቱን ለማጽዳት፣ የእስራኤል ቤት ሰዎች ሰባት ወር ሙሉ ይቀብሯቸዋል።

13. የምድሪቱ ሰዎች ሁሉ ይቀብሯቸዋል፤ እኔ የምከብርበትም ዕለት የመታሰቢያ ቀን ይሆናቸዋል፤ ይላል ጌታ እግዚአብሔር።

14. “ ‘ሰዎች ምድሪቱን ለማጽዳት በየጊዜው ይቀጠራሉ። አንዳንዶቹ ምድሪቱን ያስሳሉ፤ ከእነርሱም በተጨማሪ ሌሎች ሳይቀበሩ የቀሩትን ይቀብራሉ። ከሰባት ወር በኋላም ፍለጋ ይጀምራሉ።

15. እነርሱም በምድሪቱ መካከል ሲሄዱ፣ ከእነርሱ አንዱ የሰው ዐፅም ባየ ቍጥር ምልክት ያደርግበታል፤ ይህም መቃብር ቈፋሪዎች በሐሞን ጎግ ሸለቆ እስኪቀብሩት ድረስ ነው።

16. በዚያም ሐሞና የምትባል ከተማ አለች፤ ስለዚህ ምድሯን ያጸዳሉ።’

17. “ ‘የሰው ልጅ ሆይ፤ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ ‘ማንኛውንም ዐይነት ወፍና የዱር አራዊት ሁሉ ጥራ፤ እንዲህም በላቸው፤ “ከየአቅጣጫው ተሰብስባችሁ እኔ ወደማዘጋጅላችሁ መሥዋዕት ኑ፤ ይህም በእስራኤል ተራሮች ላይ የሚሆን ታላቁ መሥዋዕት ነው። በዚያ ሥጋ ትበላላችሁ፤ ደምም ትጠጣላችሁ።

18. እንደ አውራ በግና እንደ ጠቦት፤ እንደ ፍየልና እንደ ወይፈን፣ የኀያላን ሰዎችን ሥጋ ትበላላችሁ፤ የምድርንም መሳፍንት ደም ትጠጣላችሁ፤ እነዚህ ሁሉ የሰቡ የባሳን ከብቶች ናቸው።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ሕዝቅኤል 39