ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ሕዝቅኤል 36:16-25 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

16. እንደ ገና የእግዚአብሔር ቃል እንዲህ ሲል ወደ እኔ መጣ፤

17. የሰው ልጅ ሆይ፤ የእስራኤል ሕዝብ በገዛ ምድራቸው ይኖሩ በነበረበት ጊዜ በሥራቸውና በአኗኗራቸው አረከሷት፤ ጠባያቸውም በፊቴ፣ ሴት በወር አበባዋ ወቅት እንደምትረክሰው ዐይነት ነበር።

18. ስለዚህ በምድሪቱ ላይ ደም ስላፈሰሱና በጣዖታቶቻቸው ስላረከሷት፣ መዓቴን አፈሰ ስሁባቸው።

19. በአሕዛብ መካከል በተንኋቸው፤ እነርሱም በየአገሩ ተበታተኑ፤ እንደ ጠባያቸውና እንደ ሥራቸው መጠን ፈረድሁባቸው።

20. በአሕዛብ መካከል በሄዱበት ሁሉ ቅዱስ ስሜን አረከሱ፤ ስለ እነርሱ፣ ‘እነዚህ የእግዚአብሔር ሕዝብ ናቸው፤ ዳሩ ግን የእርሱን ምድር ትተው እንዲሄዱ ተገደዱ’ ተብሎአልና።

21. የእስራኤል ቤት በሄዱበት በአሕዛብ መካከል ሁሉ፣ ስላረከሱት ቅዱስ ስሜ ገዶኛል።

22. “ስለዚህ ለእስራኤል ቤት እንዲህ በል፤ ‘ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ “የእስራኤል ቤት ሆይ፤ ይህን ሁሉ የማደርገው ስለ እናንተ ብዬ ሳይሆን፣ በየሄዳችሁባቸው አሕዛብ መካከል ስላረከሳችሁት ስለ ቅዱስ ስሜ ስል ነው።

23. በአሕዛብ መካከል የረከሰውን፣ እናንተ በእነርሱ ዘንድ ያረከሳችሁትን፣ የታላቁን ስሜን ቅድስና አሳያለሁ፤ ከዚያም ዐይኖቻቸው እያዩ፣ በእናንተ አማካይነት ራሴን ቅዱስ አድርጌ ስገልጥ፣ አሕዛብ እኔ እግዚአብሔር እንደሆንሁ ያውቃሉ፤ ይላል ጌታ እግዚአብሔር።”

24. “ ‘ከአሕዛብ መካከል አስወጣችኋለሁ፤ ከየአገሩ ሁሉ እሰበስባችኋለሁ፤ ወደ ገዛ ምድራችሁም መልሼ አመጣችኋለሁ።

25. ንጹሕ ውሃ እረጫችኋለሁ፤ እናንተም ንጹሕ ትሆናላችሁ፤ ከርኵሰታችሁ ሁሉና ከጣዖታቶቻችሁ ሁሉ አነጻችኋለሁ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ሕዝቅኤል 36