ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ሕዝቅኤል 17:1-14 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. የእግዚአብሔር ቃል እንዲህ ሲል ወደ እኔ መጣ፤

2. “የሰው ልጅ ሆይ፤ እንቆቅልሽ አቅርብ፤ ለእስራኤልም ቤት በተምሳሌት ተናገር፤

3. እንዲህም በል፤ ‘ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ ትልቅ ክንፍና ረጅም ማርገብገቢያ ያለው እንዲሁም አካሉ በላባ የተሸፈነ መልኩ ዥጒርጒር የሆነ ታላቅ ንስር ወደ ሊባኖስ መጥቶ የዝግባ ዛፍ ጫፍ ያዘ፤

4. ከጫፉም የላይኛውን ቀንበጥ ቀንጥቦ ወደ ነጋዴዎች ምድር ወሰደ፤ በሸቀጥ ነጋዴዎችም ከተማ ተከለው።

5. “ ‘ከዚህ በኋላ ከምድሪቱ ዘር ወስዶ በመልካም ዐፈር አኖረው፤ ውሃ እንደ ልብ ባለበት ቦታ አጠገብ እንደ አኻያ ዛፍ ተከለው፤

6. በበቀለም ጊዜ አጭርና ወደ ጐን የተንሰራፋ የወይን ተክል ሆነ፤ ቅርንጫፎቹም ወደ እርሱ አቅጣጫ ዐደጉ፤ ሥሮቹ ግን እዚያው ከበታቹ ቀሩ። ስለዚህ የወይን ተክል ሆነ፤ ቅርንጫፎችን አወጣ፤ ለምለም ቅጠሎችንም አበቀለ።

7. “ ‘ደግሞም ትልቅ ክንፍ ያለውና አካሉ በላባ የተሸፈነ ሌላ ታላቅ ንስር ነበር። ያ የወይን ተክልም ውሃ ለማግኘት ከተተከለበት ቦታ ሥሩን ወደ እርሱ ሰደደ፤ ቅርንጫፉንም ወደ እርሱ ዘረጋ።

8. ቅርንጫፍ እንዲያወጣ፣ ፍሬ እንዲያፈራና ያማረ የወይን ተክል እንዲሆን በአጠገቡ ብዙ ውሃ ባለበት በመልካም መሬት ተተክሎ ነበር።”

9. “እንዲህም በላቸው፣ ‘ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ ያድግ ይሆን? ይጠወልግ ዘንድ ሥሩ ተነቅሎ ፍሬው አይረግፍምን? ቀንበጡም ሁሉ ይደርቃል። ከሥሩ ለመንቀል ብርቱ ክንድና የብዙ ሰው ጒልበት አያስፈልገውም።

10. በሌላ ስፍራ ቢተከልስ ይጸድቅ ይሆን? የምሥራቅ ነፋስ ሲመታውስ ባደ ገበት ስፍራ ፈጽሞ አይደርቅምን?’ ”

11. የእግዚአብሔር ቃል እንዲህ ሲል ወደ እኔ መጣ፤

12. “ለዚህ ዐመፀኛ ቤት እንዲህ በል፤ ‘የእነዚህ ነገሮች ትርጒም ምን እንደሆነ አታውቁምን?’ እንዲህ በላቸው፤ ‘የባቢሎን ንጉሥ ወደ ኢየሩሳሌም ሄደ፤ ንጉሥዋንና መሳፍንቷን ማረከ፤ ወደ ባቢሎንም ይዞአቸው ተመለሰ።

13. ከንጉሣውያን ቤተ ሰብ አንዱን ወስዶ ከእርሱ ጋር ውል አደረገ፤ በመሐላም ቃል አስገባው፤ የምድሪቱንም ታላላቅ ሰዎች ማርኮ ወሰደ፤

14. ይኸውም የምድሪቱ መንግሥት ተዋርዳ የእርሱን ውል በመጠበቅ ብቻ እንድትኖር እንጂ፣ ዳግመኛ እንዳታንሰራራ ለማድረግ ነበር።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ሕዝቅኤል 17