ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ሕዝቅኤል 14:8-19 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

8. ፊቴን በክፋት ወደዚያ ሰው እመልሳለሁ፤ መቀጣጫና መተረቻ አደርገዋለሁ፤ ከሕዝቤም መካከል አስወግደዋለሁ፤ በዚያን ጊዜ እኔ እግዚአብሔር እንደሆንሁ ታውቃላችሁ።

9. “ ‘ነቢዩ ትንቢት ይናገር ዘንድ ቢታለል፣ ያንን ነቢይ ያታለልሁ እኔ እግዚአብሔር ነኝ፤ ክንዴን በእርሱ ላይ አነሣለሁ፤ ከሕዝቤ ከእስራኤል መካከልም አጠፋዋለሁ።

10. በደላቸው በራሳቸው ላይ ይሆናል፤ ነቢዩም እርሱን ሊጠይቀው ከመጣው ሰው ጋር እኩል በደለኛ ይሆናል።

11. ከእንግዲህ የእስራኤል ሕዝብ መንገድ ስቶ ከእኔ አይለይም፤ ተመልሶም በኀጢአቱ ሁሉ ራሱን አያረክስም። እነርሱ ሕዝቤ ይሆናሉ፤ እኔም አምላካቸው እሆናለሁ፤ ይላል ጌታ እግዚአብሔር።”

12. የእግዚአብሔር ቃል እንዲህ ሲል ወደ እኔ መጣ፤

13. “የሰው ልጅ ሆይ፤ አንድ አገር በእኔ ባለመታመን ቢበድለኝና እኔም እጄን በላዩ ዘርግቼ የምግብ ምንጩን ባደርቅ፣ ራብንም አምጥቼበት ሰውንና እንስሳቱን ብገድል፣

14. ኖኅ፣ ዳንኤልና ኢዮብ እነዚህ ሦስቱ በዚያ ቢኖሩ እንኳ፣ በጽድቃቸው የሚያድኑት ራሳቸውን ብቻ ነው፤ ይላል ጌታ እግዚአብሔር።

15. “የዱር አራዊትንም በአገሪቱ ላይ ሰድጄ አገሪቱን ሕፃናት አልባ ቢያደርጓትና ከአራዊቱም የተነሣ ምድሪቱ ሰው እስከማያልፍባት ባድማ ብትሆን፣

16. ‘በሕያውነቴ እምላለሁ!’ ይላል ጌታ እግዚአብሔር፤ እነዚህ ሦስቱ ሰዎች ቢኖሩባት እንኳ፣ ወንዶች ወይም ሴቶች ልጆቻቸውን ማዳን አይችሉም፤ እነርሱ ብቻ ይድናሉ፤ ምድሪቱ ግን ባድማ ትሆናለች።’

17. “ሰይፍን በአገሪቱ ላይ አምጥቼ፣ ‘ሰይፍ በዚህ ምድር ይለፍ’ ብል፣ ሰውንና እንስሳን ባጠፋ፣

18. በሕያውነቴ እምላለሁ ይላል እግዚአብሔር፤ እነዚህ ሦስት ሰዎች ቢኖሩባትም እንኳ ራሳቸው ብቻ ይድናሉ እንጂ ወንዶች ወይም ሴቶች ልጆቻቸውን ማዳን አይችሉም።

19. “ቸነፈርንም በምድሪቱ ላይ ብሰድና ደም በማፍሰስ መዓቴን አውርጄ ሰውንና እንስሳን ባጠፋ፣

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ሕዝቅኤል 14