ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

2 ዜና መዋዕል 28:1-8 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. አካዝ መንገሥ በጀመረ ጊዜ ዕድሜው ሃያ ዓመት ነበር፤ በኢየሩሳሌም ተቀምጦም ዐሥራ ስድስት ዓመት ገዛ። እርሱም በእግዚአብሔር ፊት ቅን ነገር እንዳደረገው እንደ አባቱ እንደ ዳዊት አላደረገም።

2. በእስራኤል ነገሥታት መንገድ ሄደ፤ በኣሊምን ለማምለክም የተቀረጹ ጣዖታትን ሠራ።

3. እግዚአብሔር ከእስራኤላውያን ፊት ያስወገዳቸውን አሕዛብ ልማድ በመከተል፣ በሄኖም ልጅ ሸለቆ ዐጠነ፤ ወንዶች ልጆቹንም የሚቃጠል መሥዋዕት አድርጎ አቀረበ።

4. በኰረብታ መስገጃዎችና በተራሮች አናት ላይ፣ በየዛፉም ጥላ ሥር መሥዋዕት አቀረበ፤ ዕጣንም ዐጠነ።

5. ስለዚህ አምላኩ እግዚአብሔር ለሶርያ ንጉሥ አሳልፎ ሰጠው፤ ሶርያውያንም ድል አደረጉት፤ ከሕዝቡም ብዙዎቹን ምርኮኞች አድርገው ወደ ደማስቆ ወሰዷቸው። ደግሞም ለእስራኤል ንጉሥ አልፎ ተሰጠ፤ እርሱም ከባድ ጒዳት አደረሰበት።

6. ይሁዳ የአባቶቹን አምላክ እግዚአብሔርን ስለ ተወ፣ የሮሜልዩ ልጅ ፋቁሔ በአንድ ቀን ከይሁዳ መቶ ሃያ ሺህ ወታደሮች ገደለ።

7. ጦረኛው ኤፍሬማዊ ዝክሪም የንጉሡን ልጅ መዕሤያን፣ የቤተ መንግሥቱ ኀላፊ የሆነውን ዓዝሪቃምንና ለንጉሡ በማዕረግ ሁለተኛ ሰው የሆነውን ሕልቃናን ገደለ።

8. እስራኤላውያንም ከገዛ ወገኖቻቸው ሁለት መቶ ሺ ባለ ትዳር ሴቶችን፣ ወንዶችና ሴቶች ልጆችን ማረኩ፤ እንዲሁም እጅግ ብዙ ምርኮ ይዘው ወደ ሰማርያ ተመለሱ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 2 ዜና መዋዕል 28