ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

2 ዜና መዋዕል 24:1-12 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. ኢዮአስ በነገሠ ጊዜ ዕድሜው ሰባት ዓመት ነበር፤ በኢየሩሳሌም ተቀምጦም አርባ ዓመት ገዛ። እናቱ ሳብያ የተባለች የቤርሳቤህ ሴት ነበረች።

2. ካህኑ ዮዳሄ በሕይወት በነበረበት ዘመን ሁሉ፣ ኢዮአስ እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝ ነገር አደረገ።

3. ዮዳሄ ሁለት ሚስቶች መረጠለት፤ ወንዶችና ሴቶች ልጆችም ወለደ።

4. ከጥቂት ጊዜ በኋላ ኢዮአስ የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ለማደስ ወሰነ።

5. ካህናቱንና ሌዋውያኑን ሰብስቦም፣ “ወደ ይሁዳ ከተሞች ሄዳችሁ የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ በየዓመቱ ለማደስ ገንዘብ ከእስራኤል ሁሉ ሰብስቡ፤ ይህንንም አሁኑኑ አድርጉት” አላቸው። ሌዋውያኑ ግን ቸል አሉ።

6. ስለዚህ ንጉሡ ሊቀ ካህኑን ዮዳሄን ጠርቶ፣ “የእግዚአብሔር ባሪያ ሙሴና የእስራኤል ጉባኤ ለምስክሩ ድንኳን እንዲወጣ የወሰኑትን ግብር ከይሁዳና ከኢየሩሳሌም እንዲያመጡ ሌዋውያኑን ያላተጋሃቸው ለምንድን ነው?” አለው።

7. በዚህ ጊዜ የዚያች ክፉ የጎቶልያ ልጆች የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ሰብረው በመግባት የተቀደሱ ዕቃዎች እንኳ ሳይቀሩ፣ ለበኣል ጣዖታት አገልግሎት እንዲውሉ አድርገው ነበር።

8. በንጉሡም ትእዛዝ የገንዘብ መሰብሰቢያ ሣጥን ሠርተው በእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ መግቢያ በር አጠገብ በውጭ በኩል አኖሩት።

9. ከዚህ በኋላ እስራኤል በምድረ በዳ ሳሉ የእግዚአብሔር ባሪያ ሙሴ ያዘዘውን ግብር ለእግዚአብሔር እንዲያመጡ በይሁዳና በኢየሩሳሌም ዐዋጅ ተነገረ።

10. ሹማምቱ ሁሉ፣ ሕዝቡም ሁሉ ግብሩን በደስታ አመጡ፤ እስኪሞላም ድረስ በሣጥኑ ውስጥ ጨመሩ።

11. ሣጥኑ በሌዋውያኑ እጅ ወደ ንጉሡ ሹማምት በሚደርስበት ጊዜ፣ እነርሱም በውስጡ ብዙ ገንዘብ መኖሩን በሚያዩበት ጊዜ ሁሉ፣ የቤተ መንግሥቱ ጸሓፊና የሊቀ ካህናቱ ሹም ይመጡና ሣጥኑን አጋብተው ወደ ቦታው ይመልሱት ነበር። ይህን በየቀኑ በማድረግ እጅግ ብዙ ገንዘብ ሰበሰቡ።

12. ንጉሡና ዮዳሄም የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ሥራ እንዲያሠሩ ለተመደቡት ሰዎች ገንዘቡን አስረከቧቸው፤ እነርሱም የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ለማደስ ድንጋይ ጠራቢዎችንና ዐናጢዎችን እንዲሁም ቤተ መቅደሱን ለመጠገን የብረትና የናስ ሠራተኞችን ቀጠሩ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 2 ዜና መዋዕል 24