ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

2 ዜና መዋዕል 12:1-8 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. ሮብዓም መንግሥቱን ከመሠረተና ካጸና በኋላ እርሱና እስራኤል ሁሉ የእግዚአብሔርን ሕግ ተዉ።

2. እግዚአብሔርን ከመበደላቸው የተነሣም፣ ሮብዓም በነገሠ በአምስተኛው ዓመት የግብፅ ንጉሥ ሺሻቅ በኢየሩሳሌም ላይ ዘመተ።

3. ከግብፅ አብረውት የመጡትን ዐሥራ ሁለት ሺህ ሠረገላዎች፣ ስድሳ ሺ ፈረሰኞችና ስፍር ቊጥር የሌላቸውን የሊብያ፣ የሱኪምና የኢትዮጵያ ወታደሮችን ይዞ፣

4. የተመሸጉትን የይሁዳ ከተሞች በቁጥጥሩ ሥር በማድረግ እስከ ኢየሩሳሌም ዘለቀ።

5. ከዚህ በኋላ ነቢዩ ሸማያ ወደ ሮብዓምና ሺሻቅን ፈርተው በኢየሩሳሌም ወደ ተሰበሰቡት ወደ እስራኤል መሪዎች መጥቶ፣ “እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ ‘እናንተ ትታችሁኛል፤ ስለዚህ እኔም በሺሻቅ እጅ ትቼአችኋለሁ’ ” አላቸው።

6. የእስራኤል መሪዎችና ንጉሡ ራሳቸውን በማዋረድ፣ “እግዚአብሔር ጻድቅ ነው” አሉ።

7. እግዚአብሔርም ራሳቸውን እንዳዋረዱ ባየ ጊዜ፣ የእግዚአብሔር ቃል እንዲህ ሲል ወደ ሸማያ መጣ፤ “ራሳቸውን ዝቅ አድርገው ስላዋረዱ እታደጋቸዋለሁ እንጂ አላጠፋቸውም፤ ቊጣዬም በሺሻቅ እጅ በኢየሩሳሌም ላይ አይፈስስም።

8. ይሁን እንጂ እኔን በማገልገልና የሌሎችን አገሮች ነገሥታት በማገልገል መካከል ያለውን ልዩነት ያውቁ ዘንድ፣ ለእርሱ ይገዛሉ።”

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 2 ዜና መዋዕል 12