ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

1 ዜና መዋዕል 6:50-66 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

50. የአሮን ዘሮች እነዚህ ነበሩ፤ልጁ አልዓዛር፣ ልጁ ፊንሐስ፣ልጁ አቢሱ

51. ልጁ ቡቂ፣ልጁ ኦዚ፣ ልጁ ዘራእያ፣

52. ልጁ መራዮት፣ ልጁ አማርያ፣ልጁ አኪጦብ፣

53. ልጁ ሳዶቅ፣ልጁ አኪማአስ።

54. መኖሪያዎቻቸው እንዲሆኑ የተመደቡላቸው ቦታዎች እነዚህ ናቸው፤ የመጀመሪያው ዕጣ የእነርሱ ስለ ሆነ፣ ከቀዓት ጐሣ ለሆኑት ለአሮን ዘሮች የተመደቡላቸው መኖሪያዎች እነዚህ ነበሩ።

55. ለእነርሱም በይሁዳ ምድር የምትገኘው ኬብሮንና በዙሪያዋ ያለው የግጦሽ ቦታ ተሰጠ፤

56. በኬብሮን ዙሪያ የሚገኙት የዕርሻ ቦታዎችና መንደሮች ግን ለዮፎኒ ልጅ ለካሌብ ተሰጡ።

57. ለአሮን ዘሮች የመማፀኛ ከተሞች የሆኑትን ኬብሮንን፣ ልብናን፣ የቲርን፣ ኤሽትሞዓን፣

58. ሖሎንን፣ ዳቤርን፣

59. ዓሳንን፣ ዮታን፣ ቤትሳሚስን ከነመሰማሪያዎቻቸው ሰጡ።

60. ከብንያም ነገድ ድርሻ ላይ ገባዖንን፣ ጌባን፣ ጋሌማን፣ ዓናቶትን ከነመሰማሪያዎቻቸው ሰጡ።ለቀዓት ዘሮች የተከፋፈሉት እነዚህ ከተሞች ባጠቃላይ ዐሥራ ሦስት ናቸው።

61. ለቀሩት የቀዓት ዘሮች ደግሞ ከምናሴ ነገድ እኩሌታ ድርሻ ዐሥር ከተሞች ተሰጧቸው።

62. ለጌድሶን ነገድ በየጐሣቸው ከይሳኮር፣ ከአሴር፣ ከንፍታሌምና በባሳን ከሚገኘው ከምናሴ ነገድ ድርሻ ላይ ዐሥራ ሦስት ከተሞች ተመደቡላቸው።

63. ለሜራሪ ዘሮች በየጐሣቸው ከሮቤል፣ ከጋድና ከዛብሎን ድርሻ ላይ ዐሥራ ሁለት ከተሞች ተመደቡላቸው።

64. እስራኤላውያንም ከተሞቹን በዚሁ ሁኔታ መድበው ከነመሰማሪያዎቻቸው ለሌዋውያኑ ሰጧቸው።

65. ቀደም ብለው የተጠቀሱትንም ከተሞች ከይሁዳ፣ ከስምዖንና ከብንያም ነገድ ላይ ወስደው መደቡላቸው።

66. ለአንዳንድ የቀዓት ጐሣዎችም ከኤፍሬም ነገድ ድርሻ ላይ የሚኖሩበት ቦታ ተሰጣቸው።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 1 ዜና መዋዕል 6