ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

1 ዜና መዋዕል 21:21-29 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

21. ዳዊት ወደ እርሱ እየቀረበ መጣ፤ ኦርና ቀና ብሎ ሲመለከት፣ ዳዊትን አየው፤ ከዐውድማውም ወጥቶ መሬት ላይ ለጥ ብሎ በመደፋት ለዳዊት እጅ ነሣ።

22. ዳዊትም፣ “በሕዝቡ ላይ የወረደው መቅሠፍት እንዲወገድ ለእግዚአብሔር መሠዊያ እሠራ ዘንድ ዐውድማህን ልውሰደው፤ ሙሉውን ዋጋ እከፍልሃለሁ” አለው።

23. ኦርናም ዳዊትን፣ “እንዲሁ ውሰደው፤ ጌታዬ ንጉሥ ደስ ያለውን ያድርግ፤ እነሆ፤ ለሚቃጠል መሥዋዕት በሬዎቹን፣ መውቂያ በትሮቹን ለማቀጣጠያ ዕንጨት፣ ስንዴውን ደግሞ ለእህል ቍርባን እንዲሆን እሰጣለሁ፤ ሁሉንም እኔ እሰጣለሁ።” አለ።

24. ንጉሥ ዳዊት ግን ለኦርና “አይደረግም፤ ሙሉውን ዋጋ እኔ እከፍላለሁ፤ የአንተ የሆነውን ለእግዚአብሔር ለማቅረብ አልፈልግም፤ ዋጋ ያልከፈልሁበትንም የሚቃጠል መሥዋዕት አድርጌ አላቀርብም” ሲል መለሰለት።

25. ስለዚህ ዳዊት ለኦርና የቦታውን ዋጋ ስድስት መቶ ሰቅል ወርቅ ከፈለ።

26. ዳዊትም በዚያ ለእግዚአብሔር መሠዊያ ሠርቶ የሚቃጠል መሥዋዕትና የኅብረት መሥዋዕት አቀረበ። እግዚአብሔርንም ጠራ፤ እግዚአብሔርም የሚቃጠል መሥዋዕት በሚቀርብበት መሠዊያ ላይ ከሰማይ በእሳት መለሰለት።

27. ከዚያም እግዚአብሔር ለመልአኩ ተናገረ፤ መልአኩም ሰይፉን ወደ አፎቱ መለሰ።

28. በዚያን ጊዜ ዳዊት፣ እግዚአብሔር በኢያቡሳዊው በኦርና ዐውድማ ላይ እንደ መለሰለት ሲያይ፣ በዚያው ቦታ መሥዋዕት ማቅረብ ጀመረ።

29. ሙሴ በምድረ በዳ የሠራው የእግዚአብሔር ማደሪያ ድንኳንና የሚቃጠል መሥዋዕት የሚቀርብበት መሠዊያ በዚያ ጊዜ በገባዖን ኮረብታ ላይ ነበረ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 1 ዜና መዋዕል 21