ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

1 ነገሥት 8:48-65 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

48. እንዲሁም ማርከው በወሰዷቸው ጠላቶቹ ምድር ሳሉ በፍጹም ልባቸውና በፍጹም ነፍሳቸው ወደ አንተ ቢመለሱ፣ ለአባቶቻቸው ወደ ሰጠሃት ወደዚህች ምድር ወደ መረጥሃትም ወደዚህች ከተማና እኔም ለስምህ ወደ ሠራሁት ቤተ መቅደስ ፊታቸውን መልሰው ቢጸልዩ፣

49. ከማደሪያህ ከሰማይ ሆነህ ጸሎታቸውን ስማ፤ ልመናቸውንም ተቀበል፤ ርዳቸውም።

50. በአንተ ላይ ስለሠሩት ኀጢአት፣ አንተንም ስለ በደሉህ በደል ሁሉ ሕዝብህን ይቅር በል፤ የማረኳቸውም እንዲራሩላቸው አድርግ።

51. ከዚያች እንደ ብረት ማቅለጫ እቶን እሳት ከሆነችው፣ ከግብፅ ምድር ያወጣሃቸው ሕዝብህም ርስትህም ናቸውና።

52. “አሁንም ዐይኖችህ ለባሪያህና ለሕዝብህ ለእስራኤል ልመና የተከፈቱ ይሁኑ፤ ወደ አንተ በሚጮኹበትም ጊዜ ሁሉ ስማቸው፤

53. አምላኬ እግዚአብሔር ሆይ፤ አባቶቻችንን ከግብፅ ባወጣህ ጊዜ፣ በባሪያህ በሙሴ አማካኝነት እንደ ተናገርኸው ሁሉ፣ ርስትህ ይሆኑ ዘንድ ከምድር ሕዝቦች ሁሉ ለይተሃቸዋልና።”

54. ሰሎሞንም ይህን ሁሉ ጸሎትና ልመና ለእግዚአብሔር አቅርቦ ከፈጸመ በኋላ፣ እጆቹን ወደ ሰማይ በመዘርጋት፣ በጒልበቱ ተንበርክኮ ከነበረበት ከእግዚአብሔር መሠዊያ ፊት ተነሣ።

55. ከዚያም ቆሞ መላውን የእስራኤልን ጉባኤ ከፍ ባለ ድምፅ እንዲህ ሲል መረቀ፤

56. “በሰጠው ተስፋ መሠረት ለሕዝቡ ለእስራኤል ዕረፍትን ለሰጠ እግዚአብሔር ምስጋና ይግባው፤ በባሪያው በሙሴ አማካይነት ከተሰጠው መልካም ተስፋ ሁሉ አንድም ቃል አልቀረምና።

57. አምላካችን እግዚአብሔር ከአባቶቻችን ጋር እንደ ነበረ ሁሉ፣ ከእኛም ጋር ይሁን፤ አይተወን፤ አይጣለንም።

58. በመንገዱም ሁሉ እንድንሄድ፣ ለአባቶቻችን የሰጣቸውን ትእዛዞች፣ ሥርዐቶችና ደንቦች እንድንጠብቅ ልባችንን ወደ እርሱ ይመልስ።

59. በየዕለቱም ባሪያውንና ሕዝቡን እስራኤልን በሚያስፈልጋቸው ሁሉ እንዲረዳቸው፣ ይህች በእግዚአብሔር ፊት ያቀረብኋት የራሴ ልመና በቀንና በሌሊት ወደ አምላካችን ወደ እግዚአብሔር ፊት ትቅረብ።

60. ይኸውም የምድር ሕዝቦች ሁሉ እግዚአብሔር ብቻ አምላክ እንደሆነና ከእርሱ በቀር ሌላ እንደሌለ ያውቁ ዘንድ ነው።

61. ስለዚህ እንደ ዛሬው ዕለት ሁሉ፣ በሥርዐቱ እንድትኖሩና ትእዛዙን እንድትጠብቁ ልባችሁ ለአምላካችሁ ለእግዚአብሔር የተገዛ ይሁን።”

62. ከዚያም ንጉሡና ከእርሱ ጋር ያሉት እስራኤል ሁሉ በእግዚአብሔር ፊት መሥዋዕት አቀረቡ።

63. ሰሎሞንም ሃያ ሁለት ሺህ በሬ፣ መቶ ሃያ ሺህ በግና ፍየል የኅብረት መሥዋዕት አድርጎ ለእግዚአብሔር አቀረበ፤ ንጉሡና እስራኤላውያንም ሁሉ የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ በዚህ ሁኔታ ቀደሱ።

64. በዚያኑ ዕለትም ንጉሡ በእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ፊት ለፊት ያለውን የአደባባዩን መካከለኛ ክፍል ቀደሰ፤ በዚያም የሚቃጠለውን መሥዋዕት፣ የእህል ቊርባንና የኅብረት መሥዋዕቱን ስብ አቀረበ፤ ይህን ያደረገውም በእግዚአብሔር ፊት የነበረው የናስ መሠዊያ ከትንሽነቱ የተነሣ የሚቃጠለውን መሥዋዕት የእህሉን ቊርባንና የኅብረት መሥዋዕቱን ስብ መያዝ ባለመቻሉ ነበር።

65. በዚያን ጊዜም ሰሎሞን አብረውት ካሉት የእስራኤል ሕዝብ ሁሉ ጋር፣ ማለትም ከሐማት መተላለፊያ እስከ ግብፅ ደረቅ ወንዝ ካለው ምድር ከተሰበሰበው ታላቅ ጉባኤ ጋር በዓሉን አከበረ። እነርሱም ሰባት ቀን፣ በተጨማሪም ሌላ ሰባት ቀን በድምሩ ዐሥራ አራት ቀን በአምላካችን በእግዚአብሔር ፊት በዓሉን አከበሩ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 1 ነገሥት 8