ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

1 ነገሥት 8:34-53 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

34. በሰማይ ሆነህ ስማ፤ የሕዝብህ የእስራኤልን ኀጢአት ይቅር በል፤ ለአባቶቻቸው ወደ ሰጠሃቸውም ምድር መልሰህ አግባቸው።

35. “ሕዝቡም አንተን ከመበደላቸው የተነሣ፣ ሰማዩ ተዘግቶ ዝናብ ሳይዘንብ ቢቀር፣ ወደዚህ ስፍራ ቢጸልዩና ስምህን ቢጠሩ፣ ስላስጨነቅሃቸውም ከበደላቸው ቢመለሱ፣

36. በሰማይ ሆነህ ስማ፤ የባሪያዎችህን የሕዝብህን የእስራኤልን ኀጢአት ይቅር በል፤ የሚሄዱበትን ቀናውን መንገድ አስተምራቸው፤ ርስት አድርገህ ለሕዝብህ ለሰጠሃትም ምድር ዝናብ አውርድ።

37. “በምድሪቱ ላይ ራብ ወይም ቸነፈር በሚመጣበት፣ ዋግ ወይም አረማሞ በሚከሠትበት፣ አንበጣ ወይም ኵብኵባ በሚወርድበት ወይም በምድራቸው ውስጥ ባሉት ከተሞቻቸው ጠላት ቢከባቸው እንዲሁም ማንኛውም ዐይነት ጥፋት ወይም በሽታ በሚመጣባቸው ጊዜ፣

38. ከሕዝብህ ከእስራኤል ማንኛውም ሰው የልቡን ጭንቀት ዐውቆ እጆቹን ወደዚህ ቤት በመዘርጋት ጸሎትና ልመና በሚያቀርብበት ጊዜ ሁሉ፣

39. በማደሪያህ በሰማይ ሆነህ ስማ፤ ይቅር በል፤ አድርግም። አንተ ብቻ የሰውን ሁሉ ልብ የምታውቅ ስለ ሆንህ ልቡን ለምታውቀው ለእያንዳንዱ ሰው እንደ ሥራው ሁሉ ክፈለው፤

40. ይህም እነርሱ ለአባቶቻችን በሰጠሃቸው ምድር በሚኖሩበት ጊዜ ሁሉ፣ አንተን እንዲፈሩ ነው።

41. “ከሕዝብህ ከእስራኤል ወገን ያልሆነ፣ ግን ከስምህ ታላቅነት የተነሣ ከሩቅ የመጣ የባዕድ አገር ሰው ቢኖር፣

42. ሰዎች ከሩቅ የሚመጡት ስለ ታላቁ ስምህ፣ ስለ ጠንካራዪቱ እጅህ፣ ስለ ተዘረጋችው ክንድህ ሰምተው ነውና፤ እንግዳው መጥቶ ወደዚህ ቤተ መቅደስ ቢጸልይ፣

43. አንተ በማደሪያህ በሰማይ ሆነህ ስማ፤ የጠየቀህንም ሁሉ ፈጽምለት፤ ይኸውም የምድር ሕዝቦች ሁሉ ስምህን ዐውቀው፣ ሕዝብህ እስራኤል አንተን እንደሚፈሩት ሁሉ እንዲፈሩህ፣ እኔ የሠራሁትም ይህ ቤት በስምህ መጠራቱን እንዲያውቁ ነው።

44. “ሕዝብህ ጠላታቸውን ለመውጋት አንተ ወደምትልካቸው ወደ የትኛውም ቦታ ለጦርነት በሚወጡበት ጊዜ፣ አንተ ወደ መረጥሃት ከተማና እኔ ለስምህ ወደ ሠራሁት ቤተ መቅደስ ፊታቸውን መልሰው ለእግዚአብሔር ቢጸልዩ፣

45. ጸሎትና ልመናቸውን በሰማይ ሆነህ ስማ፤ ርዳቸውም።

46. “መቼም ኀጢአት የማይሠራ የለምና ሕዝብህ በአንተ ላይ ኀጢአት ቢሠሩ አንተም ተቈጥተህ ሩቅ ወይም ቅርብ ወደ ሆነው ምድሩ ማርኮ ለሚወስደው ጠላት አሳልፈህ ብትሰጣቸው፣

47. ተማርከው በሚኖሩበት አገር ሳሉ ልባቸው ቢመለስ፣ በተማረኩበትም ምድር ሆነው ንስሓ ቢገቡና ‘ኀጢአት ሠርተናል፤ በድለናል፤ ክፉ ድርጊትም ፈጽመናል’ ብለው ቢለምኑህ፣

48. እንዲሁም ማርከው በወሰዷቸው ጠላቶቹ ምድር ሳሉ በፍጹም ልባቸውና በፍጹም ነፍሳቸው ወደ አንተ ቢመለሱ፣ ለአባቶቻቸው ወደ ሰጠሃት ወደዚህች ምድር ወደ መረጥሃትም ወደዚህች ከተማና እኔም ለስምህ ወደ ሠራሁት ቤተ መቅደስ ፊታቸውን መልሰው ቢጸልዩ፣

49. ከማደሪያህ ከሰማይ ሆነህ ጸሎታቸውን ስማ፤ ልመናቸውንም ተቀበል፤ ርዳቸውም።

50. በአንተ ላይ ስለሠሩት ኀጢአት፣ አንተንም ስለ በደሉህ በደል ሁሉ ሕዝብህን ይቅር በል፤ የማረኳቸውም እንዲራሩላቸው አድርግ።

51. ከዚያች እንደ ብረት ማቅለጫ እቶን እሳት ከሆነችው፣ ከግብፅ ምድር ያወጣሃቸው ሕዝብህም ርስትህም ናቸውና።

52. “አሁንም ዐይኖችህ ለባሪያህና ለሕዝብህ ለእስራኤል ልመና የተከፈቱ ይሁኑ፤ ወደ አንተ በሚጮኹበትም ጊዜ ሁሉ ስማቸው፤

53. አምላኬ እግዚአብሔር ሆይ፤ አባቶቻችንን ከግብፅ ባወጣህ ጊዜ፣ በባሪያህ በሙሴ አማካኝነት እንደ ተናገርኸው ሁሉ፣ ርስትህ ይሆኑ ዘንድ ከምድር ሕዝቦች ሁሉ ለይተሃቸዋልና።”

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 1 ነገሥት 8