ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

1 ነገሥት 15:17-29 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

17. የእስራኤል ንጉሥ ባኦስ ይሁዳን ለመውጋት ወጣ፤ ከዚያም ወደ ይሁዳ ንጉሥ ወደ አሳ ግዛት ማንም እንዳይገባና እንዳይወጣ ለመቈጣጠር ራማን ምሽግ አድርጎ ሠራት።

18. አሳም በእግዚአብሔር ቤትና በቤተ መንግሥቱ ግምጃ ቤት የቀረውን ብርና ወርቅ በሙሉ ወሰደ፤ ከዚያም በታማኝ ሹማምቱ እጅ በደማስቆ ይገዛ ለነበረው፣ ለጠብሪሞን ልጅ፣ የአዚን የልጅ ልጅ ለሆነው ለሶርያ ንጉሥ ለቤን ሀዳድ ላከው።

19. እንዲህም አለ፤ “በአባቴና በአባትህ መካከል የስምምነት ውል እንደ ነበረ ሁሉ፣ አሁንም በእኔና በአንተ መካከል ይኑር፤ እነሆ፣ የብርና የወርቅ ገጸ በረከት ልኬልሃለሁ። አሁንም የእስራኤል ንጉሥ ባኦስ ወደ መጣበት እንዲመለስ፣ ሄደህ ከእርሱ ጋር ያደረግኸውን የስምምነት ውል አፍርስ።”

20. ቤንሀዳድም የንጉሥ አሳን ሐሳብ ተቀብሎ፣ የጦር አዛዦቹን በእስራኤል ከተሞች ላይ አዘመተ፤ ዒዮንን፣ ዳንን፣ አቤልቤት ማዕካን እንዲሁም ንፍታሌምን ጨምሮ ጌንሳሬጥን በሙሉ ድል አደረገ።

21. ባኦስም ይህን ሲሰማ፣ በራማ የጀመረውን የምሽግ ሥራ አቁሞ ወደ ቴርሳ ተመለሰ።

22. ንጉሥ አሳ አንድም ሰው እንዳይቀር በይሁዳ ሁሉ ዐዋጅ አስነገረ፤ ከዚያም ሕዝቡ ባኦስ በራማ አስቀምጦት የነበረውን ድንጋይና ዕንጨት አጋዘ፤ ንጉሡም በዚሁ ምጽጳንና በብንያም ውስጥ ጌባን ሠራ።

23. በአሳ ዘመነ መንግሥት የተከናወነው ሌላው ነገር በሙሉ፣ ያደረገውም ሁሉና የሠራቸውም ከተሞች በይሁዳ ነገሥታት ታሪክ ተጽፈው የሚገኙ አይደሉምን? ንጉሥ አሳ በሸመገለ ጊዜ ግን እግሮቹ ታመሙ።

24. አሳ ከአባቶቹ ጋር አንቀላፋ፤ እነርሱ በተቀበሩበትም በአባቱ በዳዊት ከተማ ተቀበረ፤ ልጁ ኢዮሣፍጥም በእግሩ ተተክቶ ነገሠ።

25. በይሁዳ ንጉሥ በአሳ ዘመነ መንግሥት በሁለተኛው ዓመት የኢዮርብዓም ልጅ ናዳብ በእስራኤል ላይ ነገሠ፤ ሁለት ዓመትም ገዛ።

26. እርሱም በአባቱ መንገድ በመሄድ፣ አባቱ የሠራውንና እስራኤልም እንዲሠሩ ያደረገውን ኀጢአት በመሥራት በእግዚአብሔር ፊት ክፉ ድርጊት ፈጸመ።

27. ናዳብና መላው እስራኤል በፍልስጥኤም የምትገኘውን የገባቶንን ከተማ ከበው ሳሉ፣ ከይሳኮር ነገድ የተወለደው የአኪያ ልጅ ባኦስ ዐምፆ በመነሣት ናዳብን በገባቶን ገደለው።

28. ባኦስ ናዳብን የገደለውና በእግሩ ተተክቶ የነገሠው፣ የይሁዳ ንጉሥ አሳ በነገሠ በሦስተኛው ዓመት ነው።

29. ወዲያውኑ እንደ ነገሠም የኢዮርብዓምን ቤተ ሰብ በሙሉ ፈጀ። እግዚአብሔር በሴሎናዊው ባሪያው በአኪያ በኩል እንደ ተናገረው፣ ከኢዮርብዓም ቤተ ሰብ አንድም ሰው በሕይወት ሳያስቀር፣ ሁሉንም አጠፋቸው፤

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 1 ነገሥት 15