ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

1 ነገሥት 13:26-34 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

26. ያም ከመንገድ የመለሰው ነቢይ ይህን ሲሰማ፣ “ይህ የእግዚአብሔርን ቃል ያቃለለው ያ የእግዚአብሔር ሰው ነው፤ እግዚአብሔር ባስጠነቀቀው ቃል መሠረት አሳልፎ ሰጥቶት አንበሳ ሰብሮ ገድሎታል” አለ።

27. ከዚያም ነቢዩ ልጆቹን፣ “በሉ አህያ ጫኑልኝ” አላቸውና ጫኑለት።

28. ከዚያም ሄዶ ሬሳው መንገድ ላይ ተጋድሞ አንበሳውና አህያው በአጠገቡ ቆመው አገኘ፤ አንበሳው ሬሳውን አልበላውም፤ አህያውንም አልሰበረውም።

29. ስለዚህ፣ ነቢዩ የዚያን የእግዚአብሔር ሰው ሬሳ አንሥቶ በአህያው ላይ ጫነ፤ አልቅሶ ለመቅበርም ራሱ ወደሚኖርበት ከተማ አመጣው።

30. ከዚያም ሬሳውን በራሱ መቃብር ቀበረው፤ “አወይ ወንድሜን” እያሉም አለቀሱለት።

31. ከቀበሩትም በኋላ ልጆቹን እንዲህ አላቸው፤ “እኔም በምሞትበት ጊዜ የእግዚአብሔር ሰው በተቀበረበት መቃብር ቅበሩኝ፤ ዐጥንቶቼንም በዐጥንቶቹ አጠገብ አኑሩ።

32. በቤቴል ባለው መሠዊያ፣ በሰማርያ ከተሞችና በየኰረብታው ባሉ ማምለኪያ ስፍራዎች ላይ በእግዚአብሔር ቃል ጮኾ ያሰማው መልእክት በትክክል የሚፈጸም ነውና።”

33. ይህም ሁሉ ሆኖ ኢዮርብዓም ከክፉ መንገዱ አልተመለሰም፤ ይልቁንም በኰረብታ ማምለኪያዎች ከየትኛውም ክፍል እንደ ገና ካህናትን ይሾም ጀመር፤ ካህን ለመሆን የሚፈልገውንም ሁሉ ለየኰረብታ ማምለኪያዎቹ ለየ።

34. ይህም ኀጢአት የኢዮርብዓም ቤት እንዲወድቅና ከምድር ገጽም እንዲደመሰስ ምክንያት ሆነ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 1 ነገሥት 13