ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

1 ነገሥት 10:17-29 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

17. እንዲሁም ከተጠፈጠፈ ወርቅ ሦስት መቶ ትንንሽ ጋሻ አሠራ፤ በእያንዳንዱ ጋሻ የገባው ደግሞ ሦስት ምናን ወርቅ ነው። ንጉሡም እነዚህን የሊባኖስ ዱር በተባለው ቤተ መንግሥት አኖረ።

18. ከዚያም ንጉሡ ከዝሆን ጥርስ ትልቅ ዙፋን አሠርቶ በንጹሕ ወርቅ አስለበጠው።

19. ዙፋኑ ባለ ስድስት ደረጃ ነው፤ በስተ ኋላውም ዐናቱ ላይ ክብ ቅርጽ ሲኖረው፣ ግራና ቀኙ ባለመደገፊያ ነው፤ በመደገፊያዎቹም አጠገብ ሁለት አንበሶች ቆመዋል።

20. በስድስቱም ደረጃ ጫፍ ላይ ግራና ቀኝ ስድስት ስድስት አንበሶች ቆመዋል። ይህን የመሰለም ዙፋን በየትኛውም አገር መንግሥት ከቶ ተሠርቶ አያውቅም።

21. ንጉሥ ሰሎሞን የሚጠጣበት ዋንጫ ሁሉ የወርቅ ሲሆን፣ የሊባኖስ ዱር በተባለው ቤተ መንግሥት ውስጥ የነበረው ዕቃ በሙሉ ከንጹሕ ወርቅ የተሠራ ነበር፤ በሰሎሞን ዘመነ መንግሥት ብር ይህን ያህል ዋጋ ስላልነበረው፣ ከብር የተሠራ ዕቃ ፈጽሞ አልነበረም።

22. ንጉሡ ከኪራም መርከቦች ጋር አብረው በባሕር ላይ የሚጓዙ የተርሴስ የንግድ መርከቦች ነበሩት። እነዚህም በየሦስት ዓመቱ አንድ ጊዜ ወርቅ፣ ብርና የዝሆን ጥርስ፣ ጦጣዎችና ዝንጀሮዎች ያመጡ ነበር።

23. ንጉሥ ሰሎሞንም በሀብትና በጥበብ ከምድር ነገሥታት ሁሉ ይበልጥ ነበር።

24. ዓለሙ ሁሉ እግዚአብሔር በሰሎሞን ልብ ያኖረውን ጥበብ ለመስማት ወደ እርሱ መምጣት ይፈልግ ነበር።

25. በየዓመቱም የሚመጣውን ሰው ሁሉ የብርና የወርቅ ዕቃ፣ ልብስ፣ የጦር መሣሪያ፣ ሽቶ፣ ፈረስና በቅሎ ስጦታ አድርጎ ያመጣለት ነበር።

26. ሰሎሞን ሠረገሎችና ፈረሶች ሰበሰበ፤ አንድ ሺህ አራት መቶ ሠረገሎችና ዐሥራ ሁለት ሺህ ፈረሶች ነበሩት። እነዚህንም ሁሉ ሠረገሎች በሚያኖርበት ከተሞችና ራሱ በሚኖርበት በኢየሩሳሌም እንዲሆኑ አደረገ።

27. ንጉሡም ብሩን በየቦታው እንደሚገኝ ድንጋይ አደረገ፤ የዝግባውም ዕንጨት ብዛት በቈላ እንደሚበቅል ሾላ ሆነ።

28. የሰሎሞን ፈረሶች የመጡት ከግብፅና ከቀዌ ሲሆን፣ እነዚህንም ከቀዌ ገዝተው ያመጧቸው የቤተ መንግሥቱ ንግድ ሰዎች ነበሩ።

29. አንዱን ሠረገላ ከግብፅ የሚያመጡት በስድስት መቶ ሰቅል ብር ሲሆን፣ ፈረሱን ደግሞ በመቶ አምሳ ሰቅል ብር ያመጡ ነበር፤ ለኬጢያውያንና ለሶርያ ነገሥታትም አምጥተው ይሸጡላቸው ነበር።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 1 ነገሥት 10