ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

1 ሳሙኤል 19:8-22 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

8. እንደ ገና ሌላ ጦርነት ተነሣ፤ ዳዊትም ወጥቶ ፍልስጥኤማውያንን ወጋቸው፤ ከፊቱም እስኪሸሹ ድረስ እጅግ መታቸው።

9. ነገር ግን ሳኦል ጦሩን ይዞ በቤቱ ተቀምጦ ሳለ፣ ከእግዚአብሔር ዘንድ ክፉ መንፈስ መጣበት፤ ዳዊት በገናውን ይደረድር ነበር፣

10. ሳኦልም ከግድግዳው ጋር ሊያጣብቀው ጦሩን ወረወረበት፤ ነገር ግን ዳዊት ዘወር በማለቱ ሳኦል የወረወረው ጦር በግድግዳው ላይ ተሰካ። በዚያች ሌሊት ዳዊት ሸሽቶ አመለጠ።

11. ሳኦልም የዳዊትን ቤት ከበው በማለዳ እንዲገድሉት ሰዎችን ላከ። የዳዊት ሚስት ሜልኮል ግን፣ “ሕይወትህን ለማትረፍ በዚህች ሌሊት ካልሸሸህ፣ በነገው ቀን ትገደላለህ” ብላ አስጠነቀቀችው።

12. ሜልኮልም ዳዊትን በመስኮት አሾልካ አወረደችው፣ እርሱም ሸሽቶ አመለጠ።

13. ከዚያም ሜልኮል የጣዖት ምስል ወስዳ በዐልጋው ላይ አጋደመችው፤ በራስጌውም የፍየል ጠጒር አኖረች፤ በልብስም ሸፈነችው።

14. ሳኦል ዳዊትን እንዲይዙት ሰዎች በላከ ጊዜ ሜልኮል፣ “እርሱ ታሞአል” አለቻቸው።

15. ሳኦልም ሰዎቹ ዳዊትን እንዲያዩት መልሶ ላካቸው፤ እርሱም፣ “እገድለው ዘንድ ከነዐልጋው አምጡልኝ” አላቸው።

16. የተላኩትም ሰዎች በገቡ ጊዜ እነሆ፤ የጣዖት ምስሉ በዐልጋው ላይ ተጋድሞ በራስጌውም የፍየል ጠጒር ተደርጎለት ነበር።

17. ሳኦልም ሜልኮልን፣ “እንዲህ አድርገሽ ያታለልሽኝ፣ ጠላቴ እንዲያመልጥ የሰደድሽው ለምንድን ነው?” ሲል ጠየቃት።ሜልኮልም፣ “ ‘እንዳመልጥ እርጂኝ፤ ያለዚያ እገድልሻለሁ’ አለኝ” ብላ መለሰችለት።

18. ዳዊት ሸሽቶ ካመለጠ በኋላ፣ ወደ አርማቴም ወደ ሳሙኤል ሄደ፣ ሳኦል ያደረገበትን ሁሉ ነገረው። ከዚያም እርሱና ሳሙኤል ወደ ነዋት ሄደው ተቀመጡ።

19. ለሳኦልም፣ “እነሆ፤ ዳዊት በአርማቴም በምትገኘው በነዋት ተቀምጦአል” ብለው ነገሩት።

20. ስለዚህ ዳዊትን እንዲይዙ ሰዎችን ላከ፤ ይሁን እንጂ፣ የነቢያትም ጉባኤ በሳሙኤል መሪነት ትንቢት ሲናገሩ ባዩ ጊዜ፣ የእግዚአብሔር መንፈስ በሳኦል ሰዎች ላይ ወረደ፤ እነርሱም እንደዚሁ ትንቢት ተናገሩ።

21. ሳኦልም ይህ በተነገረው ጊዜ ሌሎች ሰዎች ላከ፤ እነርሱም ትንቢት ተናገሩ፤ ሳኦል ለሦስተኛ ጊዜ ሰዎች ላከ፣ እነርሱም ደግሞ ትንቢት ተናገሩ።

22. በመጨረሻም፣ እርሱ ራሱ ወደ አርማቴም ሄደ፤ ከዚያም በሤኩ ወዳለው ትልቅ የውሃ ማጠራቀሚያ ጒድጓድ እንደ ደረሰ፣ “ሳሙኤልና ዳዊት የት ናቸው?” ሲል ጠየቀ።አንድ ሰውም “በአርማቴም በምትገኘው በነዋት ዘራማ ናቸው” ብሎ ነገረው።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 1 ሳሙኤል 19