ምዕራፎች

  1. 1

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ፊልሞና 1 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. የክርስቶስ ኢየሱስ እስረኛ ከሆነው ከጳውሎስና ከወንድማችን ከጢሞቴዎስ፤ለውድ ወዳጃችንና አብሮን ለሚሠራው ለፊልሞና፣

2. ለእኅታችን ለአፍብያ፣ አብሮን ወታደር ለሆነው ለአርክጳ በቤትህም ላለችው ቤተ ክርስቲያን፤

3. ከእግዚአብሔር ከአባታችን፣ ከጌታም ከኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና ሰላም ለእናንተ ይሁን።

4. አንተን በጸሎቴ በማስብህ ጊዜ ዘወትር አምላኬን አመሰግናለሁ፤

5. ምክንያቱም በጌታ በኢየሱስ ያለህን እምነትና ለቅዱሳንም ሁሉ ያለህን ፍቅር ሰምቻለሁ።

6. በክርስቶስ ስላለን መልካም ነገር ሁሉ በሚገባ ትረዳ ዘንድ፣ እምነትህን ለሌሎች በማካፈል እንድትተጋ እጸልያለሁ።

7. ወንድሜ ሆይ፤ የቅዱሳንን ልብ ስላሳረፍህ ከፍቅርህ ታላቅ ደስታና መጽናናት አግኝቻለሁ።

8. ስለዚህ ማድረግ የሚገባህን እንድታደርግ አዝህ ዘንድ በክርስቶስ ድፍረት ቢኖረኝም

9. በፍቅር እለምንሃለሁ፤ እንግዲህ ሽማግሌና አሁን ደግሞ የክርስቶስ ኢየሱስ እስረኛ የሆንሁት እኔ ጳውሎስ፣

10. በእስር እያለሁ ስለ ወለድሁት ልጄ ስለ አናሲሞስ እለምንሃለሁ።

11. አስቀድሞ የሚጠቅምህ አልነበረም፤ አሁን ግን ለአንተም ሆነ ለእኔ የሚጠቅም ሰው ሆኖአል።

12. የልቤ ሰው የሆነውን እርሱን መልሼ ወደ አንተ ልኬዋለሁ።

13. ስለ ወንጌል በታሰርሁበት ጊዜ በአንተ ፈንታ ሆኖ እንዲያገለግለኝ ለራሴ ላስቀረው ፈልጌ ነበር፤

14. ነገር ግን አንተ የምታደርገውን መልካም ነገር ሁሉ በውዴታ እንጂ በግዴታ እንዳይሆን ሳላማክርህ ምንም ማድረግ አልፈልግም።

15. ምናልባት ለጥቂት ጊዜ ከአንተ የተለየው፣ ተቀብለህ ለዘለቄታው አንተ ዘንድ እንድታቈየው ነው፤

16. ከእንግዲህ ወዲህ ግን እንደ ባሪያ ሳይሆን ከባሪያ በላይ የሆነ ተወዳጅ ወንድም ነው። ለእኔ ተወዳጅ ነው፤ ለአንተ ግን በሥጋም በጌታም ይበልጥ ተወዳጅ ነው።

17. እንግዲህ እንደ ባልንጀራ ከቈጠርኸኝ እኔን እንደምትቀበለኝ አድርገህ ተቀበለው።

18. አንተን የበደለህ ነገር ቢኖር ወይም የአንተ ብድር ቢኖርበት በእኔ ላይ ቊጠረው።

19. እኔ ጳውሎስ ይህን በእጄ ጽፌልሃለሁ፤ ያለበትን እኔው እከፍልሃለሁ። አንተም ራስህ የእኔ ስለ መሆንህ ምንም አልናገርም።

20. ወንድሜ ሆይ፤ በጌታ እንድትጠቅመኝ እፈልጋለሁ፤ በክርስቶስ ልቤን አሳርፍልኝ።

21. ታዛዥ መሆንህን በመተማመን፣ ከምጠይቀውም በላይ እንደምታደርግ በማወቅ እጽፍልሃለሁ።

22. ከዚህም ሌላ፣ ጸሎታችሁ መልስ አግኝቶ ወደ እናንተ ለመምጣት ተስፋ ስለማደርግ ማረፊያ አዘጋጁልኝ።

23. ከእኔ ጋር የክርስቶስ ኢየሱስ እስረኛ የሆነው ኤጳፍራ ሰላምታ ያቀርብልሃል፤

24. እንዲሁም አብረውኝ የሚሠሩት ማርቆስ፣ አርስጥሮኮስ፣ ዴማስና ሉቃስ ሰላምታ ያቀርቡልሃል።

25. የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ ከመንፈሳችሁ ጋር ይሁን።