ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዕብራውያን 3:1-15 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. እንግዲህ የሰማያዊው ጥሪ ተካፋዮች የሆናችሁ ቅዱሳን ወንድሞች ሆይ፤ የእምነታችን ሐዋርያና ሊቀ ካህናት የሆነውን ኢየሱስን አስቡ።

2. ሙሴ በእግዚአብሔር ቤት ሁሉ ላይ ታማኝ እንደ ነበር፣ እርሱም ለሾመው ታማኝ ነበር።

3. ቤትን የሚሠራ ከቤቱ ይልቅ የሚበልጥ ክብር እንዳለው፣ ኢየሱስም ከሙሴ የሚበልጥ ክብር የተገባው ሆኖ ተገኝቶአል፤

4. እያንዳንዱ ቤት የራሱ ሠሪ አለው፤ ነገር ግን ሁሉን የሠራ እግዚአብሔር ነው።

5. ሙሴ ወደ ፊት ስለሚነገረው ነገር እየመሰከረ፣ በእግዚአብሔር ቤት ሁሉ ላይ እንደ አንድ ታማኝ አገልጋይ ነበር፤

6. ክርስቶስ ግን በእግዚአብሔር ቤት ላይ እንደ ታማኝ ልጅ ነው። እኛም የምንተማመንበትንና የምንመካበትን ተስፋ አጥብቀን ብንይዝ ቤቱ ነን።

7. ስለዚህ መንፈስ ቅዱስ እንደሚል፣“ዛሬ ድምፁን ብትሰሙ፣

8. በምድረ በዳ በፈተና ቀን፣በዐመፅ እንዳደረጋችሁት፣ልባችሁን አታደንድኑ።

9. አባቶቻችሁ በዚያ ተፈታተኑኝ፤መረመሩኝ፤ ያደረግሁትንም ሁሉ ለአርባ ዓመት አዩ።

10. በዚያም ትውልድ ላይ የተቈጣሁት ለዚህ ነበር፤እንዲህም አልሁ፤ ‘ልባቸው ሁል ጊዜ ይስታል፤መንገዴንም አላወቁም፤’

11. ስለዚህ በቍጣዬ እንዲህ ብዬ ማልሁ፤“ወደ ዕረፍቴ ከቶ አይገቡም።”

12. ወንድሞች ሆይ፤ ከእናንተ ማንም ከሕያው እግዚአብሔር የሚያስኰበልል፣ ኀጢአተኛና የማያምን ልብ እንዳይኖረው ተጠንቀቁ።

13. ነገር ግን ከመካከላችሁ ማንም በኀጢአት ተታሎ ልቡ እንዳይደነድን፣ “ዛሬ” እየተባለ ሳለ በየቀኑ እርስ በርሳችሁ ተጽናኑ።

14. በመጀመሪያ የነበረንን እምነት እስከ መጨረሻው አጽንተን ብንይዝ ከክርስቶስ ጋር ተካፋዮች እንሆናለን፤

15. ይኸውም፣“ዛሬ ድምጹን ብትሰሙ፣በዐመፅ እንዳደረጋችሁት፣አሁንም ልባችሁን አታደንድኑ” እንደ ተባለው ነው።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዕብራውያን 3