ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ሮሜ 2:1-13 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. ስለዚህ አንተ በሌላው ላይ የምትፈርድ፣ የምታመካኝበት የለህም፤ በሌላው ላይ በምትፈርድበት ነገር ሁሉ፣ ራስህን ትኰንናለህ፤ ፈራጅ የሆንኸው አንተ ያንኑ ታደርጋለህና።

2. እንደዚህ በሚያደርጉትም ላይ የእግዚአብሔር ፍርድ ትክክለኛ መሆኑን እናውቃለን።

3. እንግዲህ አንተ ሰው በሌሎች ላይ እየፈረድህ፣ ያንኑ የምታደርግ ከሆነ ከእግዚአብሔር ፍርድ የምታመልጥ ይመስልሃል?

4. ወይስ የእግዚአብሔር ቸርነት ወደ ንስሓ የሚመራህ መሆኑን ሳትገነዘብ፣ የቸርነቱን፣ የቻይነቱን የትዕግሥቱን ባለጠግነት ትንቃለህ?

5. ነገር ግን በድንዳኔህና ንስሓ በማይገባ ልብህ ምክንያት ትክክለኛ ፍርዱ ሲገለጥ በእግዚአብሔር የቊጣ ቀን በራስህ ላይ ቊጣን ታከማቻለህ።

6. እግዚአብሔር “ለእያንዳንዱ እንደ ሥራው ይሰጠዋል”፤

7. በጎ የሆነውን ጸንቶ በማድረግ ክብርን፣ ሞገስንና ዘላለማዊነትን ለሚሹ የዘላለም ሕይወት ይሰጣቸዋል።

8. ነገር ግን በራስ ወዳዶች፣ እውነትን ትተው ክፋትን በሚከተሉ ፍርድና ቊጣ ይደርስባቸዋል።

9. ክፉ በሚያደርግ በማንኛውም ሰው፣ አስቀድሞ በአይሁድ ከዚያም በአሕዛብ ላይ መከራና ጭንቀት ይሆናል፤

10. ነገር ግን በጎ ለሚሠራ ለማንኛውም፣ አስቀድሞ ለአይሁድ ከዚያም ለአሕዛብ ክብር፣ ሞገስና ሰላም ይሆንለታል፤

11. እግዚአብሔር ለማንም አያደላምና።

12. ሕግ ሳይኖራቸው ኀጢአት የሠሩ ሁሉ ያለ ሕግ ይጠፋሉ፤ ሕግ እያላቸው ኀጢአት የሠሩ በሕግ ይፈረድባቸዋል፤

13. ምክንያቱም በእግዚአብሔር ፊት ጻድቃን የሚባሉት ለሕጉ የሚታዘዙ እንጂ፣ ሕጉን የሚሰሙ አይደሉም።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ሮሜ 2