ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ራእይ 4:1-8 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. ከዚህ በኋላ እነሆ በሰማይ የተከፈተ በር አየሁ፤ ቀደም ሲል እንደ መለከት ሲናገረኝ የሰማሁት ድምፅ፣ “ወደዚህ ና፤ ከዚህም በኋላ ሊሆን የሚገባውን ነገር አሳይሃለሁ” አለ

2. እኔም ወዲያወኑ በመንፈስ ነበርሁ፤ እነሆም፤ በሰማይ ዙፋን ቆሞአል፤ በዙፋኑም ላይ የተቀመጠ ነበረ።

3. ተቀምጦም የነበረው የኢያስጲድንና የሰርዲኖን ዕንቊ ይመስል ነበር። የመረግድ ዕንቊ የመሰለ ቀስተ ደመናም ዙፋኑን ከቦት ነበር።

4. በዙፋኑ ዙሪያ ሌሎች ሃያ አራት ዙፋኖች ነበሩ፤ በእነርሱም ላይ ነጭ ልብስ የለበሱና በራሳቸውም ላይ የወርቅ አክሊል የደፉ ሃያ አራት ሽማግሌዎች ተቀምጠው ነበር።

5. ከዙፋኑም መብረቅና ድምፅ፣ ነጐድጓድም ወጣ፤ በዙፋኑ ፊት ሰባት መብራቶች ይበሩ ነበር፤ እነዚህም ሰባቱ የእግዚአብሔር መናፍስት ናቸው።

6. ደግሞም በዙፋኑ ፊት እንደ መስተዋት የጠራ የብርጭቆ ባሕር ነበረ።በዙፋኑ መካከል፣ በዙሪያውም ከፊትና ከኋላ በዐይን የተሞሉ አራት ሕያዋን ፍጡራን ነበሩ።

7. የመጀመሪያው ሕያው ፍጡር አንበሳ፣ ሁለተኛው በሬ ይመስሉ ነበር፤ ሦስተኛው የሰው ፊት የሚመስል ፊት ነበረው፤ አራተኛው ደግሞ የሚበር ንስር ይመስል ነበር።

8. አራቱም ሕያዋን ፍጡራን እያንዳንዳቸው ስድስት ስድስት ክንፎች ነበሯቸው፤ በዙሪያቸውና በውስጣቸው በዐይኖች የተሞሉ ነበሩ፤ ቀንና ሌሊትም፦“ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ፣የነበረው፣ ያለውና የሚመጣው፤ሁሉን ቻይ ጌታ አምላክ”ማለትን አያቋርጡም።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ራእይ 4