ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12
  13. 13
  14. 14
  15. 15
  16. 16
  17. 17
  18. 18
  19. 19
  20. 20
  21. 21
  22. 22

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ራእይ 22 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

የሕይወት ወንዝ

1. ከዚህ በኋላ መልአኩ ከእግዚአብሔርና ከበጉ ዙፋን የሚወጣውን እንደ መስተዋት የጠራውን የሕይወት ውሃ ወንዝ አሳየኝ፤

2. ወንዙም በከተማዪቱ አውራ መንገድ መካከል ይፈስ ነበር። በወንዙ ግራና ቀኝ በየወሩ እያፈራ ዐሥራ ሁለት ጊዜ ፍሬ የሚሰጥ የሕይወት ዛፍ ነበረ፤ የዛፉም ቅጠሎች ሕዝቦች የሚፈወሱባቸው ነበሩ።

3. ከእንግዲህ ወዲህ ርግማን ከቶ አይኖርም፤ የእግዚአብሔርና የበጉ ዙፋን በከተማዪቱ ውስጥ ይሆናል፤ አገልጋዮቹም ያመልኩታል፤

4. ፊቱን ያያሉ፤ ስሙም በግምባራቸው ላይ ይሆናል።

5. ከእንግዲህ ወዲህ ሌሊት አይኖርም፤ ጌታ አምላክ ስለሚያበራላቸው የመብራት ወይም የፀሓይ ብርሃን አያስፈልጋቸውም፤ ከዘላለም እስከ ዘላለም ይነግሣሉ።

6. መልአኩም፣ “እነዚህ ቃሎች የታመኑና እውነተኞች ናቸው። የነቢያት መናፍስት ጌታ አምላክ በቅርብ የሚሆነውን ነገር ለአገልጋዮቹ እንዲያሳይ መልአኩን ልኮአል” አለኝ።

ኢየሱስ ይመጣል

7. “እነሆ፤ ቶሎ እመጣለሁ፤ የዚህን መጽሐፍ የትንቢት ቃል የሚጠብቅ ብፁዕ ነው።”

8. እነዚህን ነገሮች የሰማሁና ያየሁ እኔ ዮሐንስ ነኝ። እነዚህን ነገሮች በሰማሁና ባየሁ ጊዜ፣ እነዚህን ነገሮች ላሳየኝ መልአክ ልሰግድ በእግሩ ሥር ተደፋሁ፤

9. እርሱ ግን፣ “ተው፤ ይህን አታድርግ እኔ ከአንተና ከወንድሞችህ ከነቢያት እንዲሁም የዚህን መጽሐፍ ቃል ከሚጠብቁት ሁሉ ጋር አገልጋይ ነኝ፤ ለእግዚአብሔር ስገድ” አለኝ።

10. እንዲህም አለኝ፤ “ጊዜው ስለ ደረሰ፣ የዚህን መጽሐፍ የትንቢት ቃል በማኅተም አትዝጋው፤

11. ዐመፀኛው በዐመፁ ይቀጥል፤ ርኩሱም ይርከስ፤ ጻድቁም ይጽደቅ፤ ቅዱሱም ይቀደስ።”

12. “እነሆ፤ ቶሎ እመጣለሁ፤ ዋጋዬ በእኔ ዘንድ አለ፤ ለእያንዳንዱም እንደ ሥራው መጠን እከፍለዋለሁ።

13. አልፋና ዖሜጋ፣ ፊተኛውና ኋለኛው፣ መጀመሪያውና መጨረሻው እኔ ነኝ።

14. “ወደ ሕይወት ዛፍ ለመድረስና በበሮቿም በኩል ወደ ከተማዪቱ ለመግባት መብት እንዲኖራቸው ልብሳቸውን የሚያጥቡ ብፁዓን ናቸው።

15. ውሾች፣ አስማተኞች፣ ሴሰኞች፣ ነፍሰ ገዳዮች፣ ጣዖት አምላኪዎች፣ ውሸትን የሚወዱና የሚያደርጉ ሁሉ በውጭ አሉ።

16. “እኔ ኢየሱስ እነዚህን ነገሮች እንዲመሰክር መልአኬን ለአብያተ ክርስቲያናት ልኬአለሁ። እኔ የዳዊት ሥርና ዘር ነኝ፣ የሚያበራም የንጋት ኮከብ ነኝ።”

17. መንፈስና ሙሽራዪቱ፣ “ና” ይላሉ፤ የሚሰማም፣ “ና” ይበል፤ የተጠማም ሁሉ ይምጣ፤ የሚፈልግም ሁሉ የሕይወትን ውሃ በነጻ ይውሰድ።

18. የዚህን መጽሐፍ የትንቢት ቃል የሚሰማውን ሁሉ አስጠነቅቃለሁ፤ ማንም በዚህ ቃል ላይ አንዳች ቢጨምር፣ እግዚአብሔር በዚህ መጽሐፍ የተጻፉትን መቅሠፍቶች ይጨምርበታል፤

19. ማንም በዚህ የትንቢት መጽሐፍ ከተጻፈው ቃል አንዳች ቢያጐድል፣ እግዚአብሔር በዚህ መጽሐፍ ከተጻፉት ከሕይወት ዛፍና ከቅድስቲቱ ከተማ ዕድሉን ያጐድልበታል።

20. እነዚህን ነገሮች የሚመሰክረው፣ “አዎ፣ ቶሎ እመጣለሁ” ይላል።አሜን፤ ጌታ ኢየሱስ ሆይ፤ ና።

21. የጌታ የኢየሱስ ጸጋ ከእግዚአብሔር ሕዝብ ጋር ይሁን፤ አሜን።