ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ራእይ 2:5-19 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

5. እንግዲህ ከየት እንደ ወደቅህ አስብ፤ ንስሓ ገብተህ ቀድሞ ታደርገው የነበረውን ነገር አድርግ፤ ንስሓ ካልገባህ፣ መጥቼ መቅረዝህን ከቦታው እወስድብሃለሁ።

6. ነገር ግን ይህ በጎ ነገር አለህ፤ እኔ የምጠላውን የኒቆላውያንን ሥራ አንተም ጠልተሃል።

7. መንፈስ ለአብያተ ክርስቲያናት የሚናገረውን፣ ጆሮ ያለው ይስማ፤ ድል ለሚነሣ በእግዚአብሔር ገነት ካለው ከሕይወት ዛፍ እንዲበላ አደርገዋለሁ።

8. “በሰምርኔስ ላለው ቤተ ክርስቲያን መልአክ እንዲህ ብለህ ጻፍ፤ የመጀመሪያውና የመጨረሻው፣ ሞቶም የነበረውና ሕያው የሆነው እንዲህ ይላል፤

9. መከራህንና ድኽነትህን ዐውቃለሁ፤ ይሁን እንጂ ሀብታም ነህ፤ አይሁድ ሳይሆኑ አይሁድ ነን እያሉ ስምህን የሚያጠፉትን ዐውቃለሁ፤ እነርሱ ግን የሰይጣን ማኅበር ናቸው።

10. ሊደርስብህ ያለውን መከራ አትፍራ። እነሆ፤ ዲያብሎስ ሊፈትናችሁ አንዳንዶቻችሁን ወደ እስር ቤት ይጥላል፤ ዐሥር ቀንም መከራ ትቀበላላችሁ። እስከ ሞት ድረስ ታማኝሁን፤ እኔም የሕይወትን አክሊል እሰጥሃለሁ።

11. መንፈስ ለአብያተ ክርስቲያናት የሚናገረውን ጆሮ ያለው ይስማ፤ ድል የሚነሣም በሁለተኛው ሞት ከቶ አይጐዳም።

12. “በጴርጋሞን ላለው ቤተ ክርስቲያን መልአክ እንዲህ ብለህ ጻፍ፤ በሁለት በኩል የተሳለ ስለታም ሰይፍ ያለው እንዲህ ይላል፤

13. የሰይጣን ዙፋን ባለበት እንደምትኖር ዐውቃለሁ፤ ሆኖም ስሜን አጥብቀህ ይዘሃል። ሰይጣን በሚኖርበት በእናንተ ከተማ የተገደለው ታማኙ ምስክሬ አንቲጳስ በነበረበት ዘመን እንኳ፣ በእኔ ያለህን እምነት አልካድህም።

14. ይሁን እንጂ የምነቅፍብህ ጥቂት ነገር አለኝ፤ የእስራኤል ልጆች ለጣዖት የተሠዋ ምግብ እንዲበሉና እንዲሴስኑ በፊታቸው መሰናከያ ያስቀምጥ ዘንድ ባላቅን ያስተማረውን የበለዓምን ትምህርት የሚከተሉ አንዳንድ ሰዎች በመካከልህ አሉ፤

15. የኒቆላውያንን ትምህርት የሚከተሉ ሰዎችም በአንተ ዘንድ አሉ።

16. ስለዚህ ንስሓ ግባ፤ አለዚያ ቶሎ እመጣብሃለሁ፤ በአፌም ሰይፍ እዋጋቸዋለሁ።

17. መንፈስ ለአብያተ ክርስቲያናት የሚናገረውን ጆሮ ያለው ይስማ፤ ድል ለሚነሣ ከተሰወረው መና እሰጠዋለሁ፤ ደግሞም ከሚቀበለው ሰው በስተቀር ማንም የማያውቀውን አዲስ ስም የተጻፈበት ነጭ ድንጋይ እሰጠዋለሁ።

18. “በትያጥሮን ላለው ቤተ ክርስቲያን መልአክ እንዲህ ብለህ ጻፍ፤ እንደ እሳት ነበልባል የሆኑ ዐይኖችና በእሳት ቀልጦ የነጠረ ናስ የሚመስሉ እግሮች ያሉት የእግዚአብሔር ልጅ እንዲህ ይላል፤

19. ሥራህን፣ ፍቅርህን፣ እምነትህን፣ አገልግሎትህንና ትዕግሥትህን ዐውቃለሁ፤ ደግሞም ከመጀመሪያው ሥራህ ይልቅ የአሁኑ እንደሚበልጥ ዐውቃለሁ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ራእይ 2