ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ራእይ 15:1-8 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. ሌላም ታላቅና አስደናቂ ምልክት በሰማይ አየሁ፤ የመጨረሻዎቹን ሰባት መቅሠፍቶች የያዙ ሰባት መላእክት አየሁ፤ የመጨረሻ የተባሉትም የእግዚአብሔር ቊጣ የሚፈጸመው በእርሱ በመሆኑ ነው።

2. ከእሳት ጋር የተቀላቀለ የብርጭቆ ባሕር የሚመስል አየሁ፤ በባሕሩም አጠገብ አውሬውን፣ ምስሉንና የስሙን ቊጥር ድል የነሡትን ቆመው አየሁ፤ እነርሱም ከእግዚአብሔር የተሰጣቸውን በገና ይዘው፣

3. የእግዚአብሔር ባሪያ የሆነውን የሙሴን መዝሙርና የበጉን መዝሙር እንዲህ እያሉ ይዘምሩ ነበር፤“ሁሉን ቻይ ጌታ አምላክ ሆይ፤ሥራህ ታላቅና አስደናቂ ነው።የዘመናት ንጉሥ ሆይ፤መንገድህ ጽድቅና እውነት ነው።

4. ጌታ ሆይ፤ አንተን የማይፈራ፣ስምህን የማያከብርስ ማን ነው?አንተ ብቻ ቅዱስ ነህና።የጽድቅ ሥራህ ስለ ተገለጠ፣ሕዝቦች ሁሉ ይመጣሉ፤በፊትህም ይሰግዳሉ።

5. ከዚህ በኋላም አየሁ፤ በሰማይ ያለው ቤተ መቅደስ፣ ይኸውም የምስክሩ ድንኳን ተከፍቶ ነበር፤

6. ሰባቱን መቅሠፍቶች የያዙት ሰባቱ መላእክት ከቤተ መቅደሱ ወጡ፤ እነርሱም ከተልባ እግር የተሠራ ንጹሕ የሚያበራ ልብስ ለብሰው፣ ደረታቸውንም በወርቅ መታጠቂያ ታጥቀው ነበር።

7. ከዚያም ከአራቱ ሕያዋን ፍጡራን አንዱ ከዘላለም እስከ ዘላለም በሚኖረው አምላክ ቊጣ የተሞሉትን ሰባት የወርቅ ጽዋዎች ለሰባቱ መላእክት ሰጣቸው።

8. ቤተ መቅደሱም ከእግዚአብሔር ክብር፣ ከኀይሉም በወጣው ጢስ ተሞላ፤ የሰባቱ መላእክት ሰባት መቅሠፍቶች እስኪፈጸሙ ድረስ ማንም ወደ ቤተ መቅደሱ መግባት አልቻለም።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ራእይ 15