ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ሉቃስ 21:16-28 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

16. ወላጆቻችሁ፣ ወንድሞቻችሁ፣ ዘመዶቻችሁና ጓደኞቻችሁ እንኳ ሳይቀሩ አሳልፈው ይሰጡአችኋል፤ ከእናንተም አንዳንዶቹን ይገድላሉ፤

17. ስለ ስሜም በሰዎች ሁሉ ዘንድ የተጠላችሁ ትሆናላችሁ።

18. ነገር ግን ከራሳችሁ ጠጒር አንዷ እንኳ አትጠፋም፤

19. ጸንታችሁም በመቆም ነፍሳችሁን ታተርፋላችሁ።

20. “ኢየሩሳሌም በጦር ሰራዊት ተከባ በምታዩበት ጊዜ፣ ጥፋቷ መቃረቡን ዕወቁ።

21. በዚያን ጊዜ በይሁዳ ያሉ ወደ ተራሮች ይሽሹ፤ በከተማ ያሉትም ከዚያ ይውጡ፤ በገጠር ያሉትም ወደ ከተማዪቱ አይግቡ፤

22. የተጻፈው ሁሉ ይፈጸም ዘንድ ይህ የበቀል ጊዜ ነውና።

23. በምድሪቱ ላይ ታላቅ መከራ ይሆናል፤ በዚህም ሕዝብ ላይ ቊጣ ይመጣል፤ ስለዚህ በዚያን ወቅት ለነፍሰ ጡሮችና ለሚያጠቡ እናቶች ወዮላቸው!

24. በሰይፍ ይወድቃሉ፤ ወደ አሕዛብም ሁሉ በምርኮ ይወሰዳሉ፤ ኢየሩሳሌምም የአሕዛብ ዘመን እስኪፈጸም ድረስ፣ በአሕዛብ የተረገጠች ትሆናለች።

25. “በፀሓይ፣ በጨረቃና በከዋክብት ላይ ምልክት ይሆናል፤ ከባሕሩና ከሞገድ ድምፅ የተነሣ፣ በምድር ላይ ያሉ ሕዝቦች ይጨነቃሉ፤ ይታወካሉም፤

26. የሰማያት ኀይላት ስለሚናወጡ፣ ሰዎች በፍርሀትና በዓለም ላይ ምን ይመጣ ይሆን እያሉ በመጠባበቅ ይዝላሉ።

27. በዚያን ጊዜ የሰው ልጅ በኀይልና በታላቅ ክብር በደመና ሲመጣ ያዩታል።

28. እናንተም እነዚህ ነገሮች መፈጸም ሲጀምሩ፣ መዳናችሁ ስለ ተቃረበ፣ ቀጥ ብላችሁ ቁሙ፤ ራሳችሁንም ወደ ላይ ቀና አድርጉ።”

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ሉቃስ 21