ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ሉቃስ 16:17-31 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

17. ነገር ግን ከሕግ አንዲት ነጥብ ከምትወድቅ ሰማይና ምድር ቢያልፍ ይቀላል።

18. “ሚስቱን ፈቶ ሌላይቱን የሚያገባ ሁሉ ያመነዝራል፤ ከባሏ የተፋታችውንም ሴት የሚያገባ ያመነዝራል።”

19. ደግሞም ኢየሱስ እንዲህ አለ፤ “ሐምራዊና ቀጭን በፍታ የለበሰ፣ በየቀኑም በተድላ ደስታ የሚኖር አንድ ሀብታም ሰው ነበረ።

20. በአንጻሩም፣ መላ ሰውነቱ በቊስል የተወረረ አንድ አልዓዛር የሚባል ድኻ በዚህ ሀብታም ሰው ደጃፍ ይተኛ ነበር፤

21. ከሀብታሙ ሰው ማእድ የወደቀውን ፍርፋሪ እንኳ ሊመገብ ይመኝ ነበር፤ ውሾችም ሳይቀሩ መጥተው ቊስሉን ይልሱ ነበር።

22. “ይህም ድኻ ሞተ፤ መላእክትም ወደ አብርሃም ዕቅፍ ወሰዱት። ሀብታሙም ሰው ደግሞ ሞቶ ተቀበረ።

23. በሲኦልም እየተሠቃየ ሳለ ቀና ብሎ ከሩቅ አብርሃምን አየ፤ አልዓዛርንም በዕቅፉ ይዞት አየ።

24. እርሱም፣ ‘አብርሃም አባት ሆይ፤ ራራልኝ፤ በዚህ ነበልባል እየተሠቃየሁ ስለ ሆነ፣ አልዓዛር የጣቱን ጫፍ ውሃ ነክሮ ምላሴን እንዲያቀዘቅዝልኝ እባክህ ላክልኝ’ እያለ ጮኸ።

25. “አብርሃም ግን እንዲህ አለው፤ ‘ልጄ ሆይ፤ አንተ በምድራዊ ሕይወትህ ዘመን መልካም ነገሮችን እንደ ተቀበልህ፣ አልዓዛርም ደግሞ ክፉ ነገሮችን እንደ ተቀበለ አስታውስ፤ አሁን ግን እርሱ እዚህ ሲጽናና፣ አንተ በሥቃይ ላይ ትገኛለህ።

26. ከሁሉም በላይ ከዚህ ወደ እናንተ ለማለፍ የሚፈልጉ እንደማይችሉ፣ እዚያ ያሉትም ደግሞ ወደ እኛ እንዳይሻገሩ፣ በእኛና በእናንተ መካከል ትልቅ ገደል ተደርጎአል።”

27. “እርሱም እንዲህ አለ፤ ‘አባት ሆይ፤ እንግዲያውስ አልዓዛርን ወደ አባቴ ቤት እንድትሰደው እለምንሃለሁ፤

28. አምስት ወንድሞች ስላሉኝ፣ እነርሱም ወደዚህ የሥቃይ ስፍራ እንዳይመጡ ያስጠንቅቃቸው።’

29. “አብርሃም ግን፣ ‘ሙሴና ነቢያት አሏቸው፤ እነርሱን ይስሙ’ አለው።

30. “እርሱም፣ ‘አብርሃም አባት ሆይ፤ እንደዚህ አይደለም፤ አንድ ሰው ከሙታን ተነሥቶ ቢሄድላቸው ንስሓ ይገባሉ’ አለ።

31. አብርሃምም፣ ‘ሙሴንና ነቢያትን የማይሰሙ ከሆነ፣ አንድ ሰው ከሙታን ቢነሣ እንኳ አያምኑም’ አለው።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ሉቃስ 16