ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

2 ጢሞቴዎስ 2:1-16 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. እንግዲህ ልጄ ሆይ፤ አንተ በክርስቶስ ኢየሱስ ባለው ጸጋ በርታ።

2. በብዙ ምስክር ፊት ከእኔ የሰማኸውን፣ ሌሎችን ለማስተማር ብቃት ላላቸው ለታመኑ ሰዎች ዐደራ ስጥ።

3. እንደ ክርስቶስ ኢየሱስ በጎ ወታደር፣ ከእኛ ጋር መከራን ተቀበል።

4. በውትድርና የሚያገለግል ሰው አዛዡን ለማስደሰት ይጥራል እንጂ በሌላ ሥራ ራሱን አያጠላ ልፍም።

5. እንደዚሁም በውድድር የሚሳተፍ ሰው፣ የውድድሩን ሕግ ጠብቆ ካልተወዳደረ የድሉን አክሊል አያገኝም።

6. ትጉህ ገበሬም ከሰብሉ ለመጠቀም የመጀመሪያው ሊሆን ይገባዋል።

7. እኔ የምለውን ልብ በል፤ ጌታ በሁሉም ነገር ማስተዋልን ይሰጥሃልና።

8. ከሙታን የተነሣውን፣ ከዳዊት ዘርም የሆነውን ኢየሱስ ክርስቶስን አስብ፤ የእኔም ወንጌል ይኸው ነው፤

9. ለዚህም እንደ ወንጀለኛ እስከ መታሰር ድረስ መከራን እየተቀበልሁ ነው፤ የእግዚአብሔር ቃል ግን አይታሰርም።

10. ስለዚህ በክርስቶስ ኢየሱስ ያለውን መዳን ከዘላለም ክብር ጋር እነርሱም ያገኙ ዘንድ፣ ለተመረጡት ስል ሁሉንም በመታገሥ እጸናለሁ።

11. እንዲህ የሚለው ቃል የታመነ ነው፤ከእርሱ ጋር ከሞትን፣ከእርሱ ጋር ደግሞ በሕይወት እንኖራለን።

12. ብንጸና፣ከእርሱ ጋር ደግሞ እንነግሣለን።ብንክደው፣እርሱ ደግሞ ይክደናል፤

13. ታማኞች ሆነን ባንገኝእርሱ ታማኝ እንደሆነ ይኖራል፤ራሱን መካድ አይችልምና።

14. ስለ እነዚህ ነገሮች ማሳሰብህን አትተው፤ በቃላት እንዳይነታረኩ በእግዚአብሔር ፊት አስጠንቅቃቸው፤ ይህ ጥቅም የሌለው፣ የሚሰሙትንም የሚያፈርስ ነውና።

15. እንደ ማያፍርና የእውነትን ቃል በትክክል እንደሚያስረዳ የተመሠከረለት ሠራተኛ፣ ራስህን በእግዚአብሔር ፊት ልታቀርብ ትጋ።

16. እግዚአብሔርን ከማያስከብር ከንቱ ልፍለፋ ራቅ፤ በዚህ ነገር የተጠመዱ ሰዎች ከእግዚአብሔር እየራቁ ይሄዳሉና።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 2 ጢሞቴዎስ 2