ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

2 ተሰሎንቄ 2:5-17 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

5. ከእናንተ ጋር በነበርሁበት ጊዜ እነዚህን ነገሮች ነግሬአችሁ እንደ ነበር ትዝ አይላችሁምን?

6. በራሱ ጊዜ ይገለጥ ዘንድ አሁን ምን እንደሚከለክለው ታውቃላችሁ።

7. የዐመፅ ምስጢር አሁንም እንኳ እየሠራ ነውና፤ ነገር ግን ይህ የሚሆነው የሚከለክለው ከመንገድ እስኪወገድ ድረስ ብቻ ነው

8. ከዚያም በኋላ ጌታ ኢየሱስ በአፉ እስትንፋስ የሚያስወግደውና በምጽአቱም ክብር ፈጽሞ የሚያጠፋው ዐመፀኛ ይገለጣል።

9. የዐመፀኛው አመጣጥ በሰይጣን አሠራር ላይ የተመሠረተ ሲሆን፣ ይህም በሐሰተኛ ታምራት በምልክቶችና በድንቅ ነገሮች ሁሉ ይሆናል፤

10. እንዲሁም ይድኑ ዘንድ እውነትን ባለመውደድ የሚጠፉትን ሰዎች በሚያታልል በተለያየ የክፋት ሥራ ይመጣል።

11. በዚህም ምክንያት እግዚአብሔር በሐሰት እንዲያምኑ የስሕተትን አሠራር ይልክባቸዋል፤

12. ይህም የሚሆነው እውነትን ያላመኑት ነገር ግን በክፋት ደስ ይላቸው የነበሩ ሁሉ እንዲፈረድባቸው ነው።

13. በጌታ የተወደዳችሁ ወንድሞች ሆይ፤ እኛ ግን ሁል ጊዜ ስለ እናንተ እግዚአብሔርን ልናመሰግን ይገባናል። ምክንያቱም እግዚአብሔር እናንተን ከመጀመሪያ አንሥቶ በመንፈስ ተቀድሳችሁና በእውነትም አምናችሁ እንድትድኑ መርጦአችኋል።

14. የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ክብር ተካፋዮች እንድ ትሆኑም በወንጌላችን አማካይነት ጠርቶአችኋል።

15. እንግዲህ ወንድሞች ሆይ፤ ጸንታችሁ ቁሙ፤ በአንደበታችንም ሆነ በመልእክታችን ያስተላለፍንላችሁን ትምህርት አጥብቃችሁ ያዙ።

16. ራሱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደግሞም እኛን የወደደንና በጸጋው የዘላለም መጽናናትና መልካም ተስፋን የሰጠን እግዚአብሔር አባታችን፣

17. ልባችሁን ያጽናኑት፤ በበጎ ሥራና በቃል ሁሉ ያበርቷችሁ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 2 ተሰሎንቄ 2