ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

1 ጢሞቴዎስ 4:1-11 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. በኋለኞች ዘመናት አንዳንዶች እምነትን ክደው አታላይ መናፍስትንና የአጋንንትን ትምህርት እንደሚከተሉ መንፈስ በግልጥ ይናገራል።

2. እንዲህ ያለው ትምህርት የሚመጣው ኅሊናቸው በጋለ ብረት የተጠበሰ ያህል ከደነዘዘባቸው ግብዝ ውሸተኞች ነው።

3. እነርሱ፣ ሰዎች እንዳያገቡ ይከለክላሉ፤ የሚያምኑና እውነትን የሚያውቁ ሰዎች እግዚአብሔር የፈጠረውን በምስጋናም የሚቀበሉትን እንዳይበሉ ያዛሉ፤

4. እግዚአብሔር የፈጠረው ማንኛውም ነገር መልካም ነውና፤ በምስጋና ከተቀበሉትም የሚጣል ምንም ነገር የለም፣

5. በእግዚአብሔር ቃልና በጸሎት የተቀደሰ ነውና።

6. ይህን ትእዛዝ ለወንድሞች ብታሳስብ፣ በእምነት ቃልና በተቀበልኸው መልካም ትምህርት ታንጸህ የክርስቶስ ኢየሱስ በጎ አገልጋይ ትሆናለህ።

7. እግዚአብሔርን ከማያከብር ርባናቢስ አፈ ታሪክና ከአሮጊቶች ተረታ ተረት ራቅ፤ ይልቁንም ለእውነተኛ መንፈሳዊ ሕይወት ራስህን አሠልጥን።

8. የአካል ብቃት ልምምድ ለጥቂት ነገር ይጠቅማልና፤ ለእውነተኛ መንፈሳዊ ሕይወት ራስን ማሠልጠን ግን ለአሁኑም ሆነ ለሚመጣው ሕይወት ተስፋ ስላለው ለሁለቱም ይጠቅማል።

9. ይህ ቃል የታመነና ሙሉ ለሙሉ ሊቀበሉት የሚገባ ነው፤

10. ለዚህ ብለን እንጥራለን፤ እንደክማለንም፤ ይኸውም ለሰዎች ሁሉ በተለይም ለሚያምኑት አዳኝ በሆነው በሕያው እግዚአብሔር ተስፋ ስለምናደርግ ነው።

11. እነዚህን ነገሮች እዘዝ፤ አስተምርም።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 1 ጢሞቴዎስ 4