ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

1 ጢሞቴዎስ 1:1-13 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. በአዳኛችን በእግዚአብሔር፣ ተስፋችንም በሆነው በክርስቶስ ኢየሱስ ትእዛዝ የክርስቶስ ኢየሱስ ሐዋርያ ከሆነው ከጳውሎስ፤

2. በእምነት እውነተኛ ልጄ ለሆነው ለጢሞቴዎስ፤ከእግዚአብሔር ከአባታችን፣ ከጌታችንም ከክርስቶስ ኢየሱስ ጸጋና ምሕረት፣ ሰላምም ይሁን።

3. ወደ መቄዶንያ በሄድሁ ጊዜ ዐደራ እንዳልሁህ፣ አንዳንድ ሰዎች ከእንግዲህ የሐሰት ትምህርት እንዳያስተምሩ ታዛቸው ዘንድ በዚያው በኤፌሶን ተቀመጥ፤

4. ደግሞም ለተረትና መጨረሻ ለሌለው የትውልዶች ታሪክ ራሳቸውን አሳልፈው እንዳይሰጡ እዘዛቸው። እነዚህ ነገሮች በእምነት ከሆነው ከእግዚአብሔር ሥራ ይልቅ ክርክርን ያነሣሣሉ።

5. የዚህ ትእዛዝ ዐላማ ግን ከንጹሕ ልብ፣ ከበጎ ኅሊና እንዲሁም ከእውነተኛ እምነት የሚገኝ ፍቅር ነው።

6. አንዳንዶች ከእነዚህ ነገሮች ዘወር ብለው ወደ ከንቱ ንግግር ተመልሰዋል።

7. የሕግ መምህራን ለመሆን ይፈልጋሉ፤ ሆኖም ስለሚናገሩት ወይም አስረግጠው ስለሚሟገቱለት ነገር አያውቁም።

8. ነገር ግን ሰው በአግባቡ ከተጠቀመበት፣ ሕግ መልካም መሆኑን እናውቃለን።

9. ደግሞም ሕግ የተሰጠው ለጻድቃን ሳይሆን፣ ለሕግ ተላላፊዎችና ለዐመፀኞች፣ ፈሪሃ እግዚአብሔር ለሌላቸውና ለኀጢአተኞች፣ ቅድስና ለሌላቸውና እግዚአብሔርን ለሚንቁ፣ አባትና እናታቸውን ለሚገድሉ፣ ለነፍሰ ገዳዮች መሆኑን እናውቃለን፤

10. እንዲሁም ለዘማውያን፣ ከወንድ ጋር ለሚተኙ ወንዶች፣ ሰውን ለሚሸጡና ለሚገዙ፣ ለውሸተኞች፣ በሐሰት ለሚምሉ፣ ጤናማ የሆነውን ትምህርት ለሚጻረሩ ሁሉ ነው፤

11. ይህ ጤናማ ትምህርት ቡሩክ እግዚአብሔር ለእኔ በዐደራ ከሰጠኝ የክብር ወንጌል ጋር የሚስማማ ነው።

12. በአገልግሎቱ በመሾም ታማኝ አድርጎ የቈጠረኝን፣ ብርታት የሰጠኝን ጌታችንን ክርስቶስ ኢየሱስን አመሰግናለሁ።

13. ምንም እንኳ ከዚህ በፊት ተሳዳቢ፣ አሳዳጅና ዐመፀኛ የነበርሁ ብሆንም፣ ባለማወቅና ባለማመን ስላደረግሁት ምሕረት ተደርጎልኛል፤

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 1 ጢሞቴዎስ 1