ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12
  13. 13
  14. 14
  15. 15
  16. 16

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

1 ቆሮንቶስ 6 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

መካሰስ በክርስቲያኖች መካከል

1. ከመካከላችሁ አንድ ሰው ከሌላው ጋር ሙግት ቢኖረው፣ ጒዳዩን በቅዱሳን ፊት በማቅረብ ፈንታ እንዴት ደፍሮ በማያምኑ ሰዎች ፊት ለመፋረድ ያቀርባል?

2. ቅዱሳን በዓለም ላይ እንደሚፈርዱ አታውቁምን? በዓለም ላይ የምትፈርዱ ከሆነ፣ እንግዲያው፣ በትንሹ ነገር ላይ ለመፍረድ አትበቁምን?

3. በምድራዊ ሕይወት ጒዳይ ቀርቶ፣ በመላእክት ላይ እንኳ እንደምንፈርድ አታውቁምን?

4. እንግዲህ እንዲህ ያለ ጒዳይ ሲያጋጥ ማችሁ፣ በቤተ ክርስቲያን የተናቁትን ሰዎች ፈራጅ አድርጋችሁ ሹሟ!

5. ይህንንም የምለው ላሳፍራችሁ ብዬ ነው። ለመሆኑ ከመካካላችሁ ወንድሞችን ለማስታረቅ የሚበቃ አስተዋይ ሰው የለምን?

6. ነገር ግን ወንድም ወንድሙን ለመክሰስ ፍርድ ቤት ይሄዳል፤ ያውም በማያምኑ ሰዎች ፊት!

7. እንግዲህ በመካከላችሁ መካሰስ መኖሩ ራሱ ውድቀታችሁን ያሳያል። ብትበደሉ አይሻልምን? ብትታለሉስ አይሻልምን?

8. እናንተ ግን ራሳችሁ ትበድላላችሁ፤ ታታልላላችሁም፤ ያውምኮ ወንድሞቻችሁን።

9. ዐመፀኞች የእግዚአብሔርን መንግሥት እንደማይወርሱ አታውቁምን? በዚህ ነገር አትታለሉ፤ ሴሰኞች፣ ጣዖት አምላኪዎች፣ አመንዝሮች፣ ወንደቃዎች፣ ግብረ ሰዶማውያን፣

10. ወይም ሌቦች፣ ስግብግቦች፣ ሰካራሞች፣ ተሳዳቢዎችና ቀማኞች የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም።

11. ከእናንተ አንዳንዶቻችሁ እንደዚህ ነበራችሁ፤ አሁን ግን በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ስምና በአምላካችን መንፈስ ታጥባችኋል፤ ተቀድሳችኋል፤ ጸድቃችኋል።

የዝሙት ኀጢአት

12. “ሁሉ ነገር ተፈቅዶልኛል፤” ይሁን እንጂ ሁሉም ነገር አይጠቅምም፤ “ሁሉ ነገር ተፈቅዶልኛል፤” ይሁን እንጂ ምንም ነገር በእኔ ላይ አይሠለጥንም።

13. ደግሞም፣ “ምግብ ለሆድ ነው፤ ሆድም ለምግብ ነው፤” እግዚአብሔር ግን ሁለቱንም ያጠፋቸዋል። ሰውነት ለጌታ ነው እንጂ ለዝሙት አይደለም፤ ጌታም ለሰውነት ነው።

14. እግዚአብሔር ጌታን ከሙታን አንዳስነሣው፣ እኛንም ደግሞ በኀይሉ ከሙታን ያስነሣናል።

15. ሰውነታችሁ የክርስቶስ የአካሉ ብልቶች እንደሆነ አታውቁምን? ታዲያ፣ የክርስቶስን ብልቶች ወስጄ ከዝሙት አዳሪ ሴት ብልቶች ጋር አንድ ላድርገውን? ከቶ አይገባም!

16. ወይስ ከዝሙት አዳሪ ጋር የሚተባበር ሰው ከእርሷ ጋር አንድ ሥጋ እንደሚሆን አታውቁምን? “ሁለቱ አንድ ሥጋ ይሆናሉ” ተብሎአልና።

17. ነገር ግን ከጌታ ጋር የሚተባበር ከእርሱ ጋር አንድ መንፈስ ይሆናል።

18. ከዝሙት ሽሹ። ሰው የሚሠራው ኀጢአት ሁሉ ከአካሉ ውጭ ነው፤ ዝሙትን የሚፈጽም ግን በገዛ አካሉ ላይ ኀጢአት ይሠራል።

19. ለመሆኑ፣ ሰውነታችሁ በውስጣችሁ የሚኖረው የመንፈስ ቅዱስ ቤተ መቅደስ እንደሆነ አታውቁምን? ይህም መንፈስ ከእግዚአብሔር የተቀበላችሁት ነው። እናንተም የራሳችሁ አይደላችሁም፤

20. በዋጋ ተገዝታችኋልና፤ ስለዚህ በሰውነታችሁ እግዚአብሔርን አክብሩ።