ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

1 ቆሮንቶስ 2:1-11 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. ወንድሞች ሆይ፤ ወደ እናንተ በመጣሁ ጊዜ፣ የእግዚአብሔርን ምስጢር በረቀቀ የንግግር ችሎታ ወይም በላቀ ጥበብ ልገልጥላችሁ አልመጣሁም።

2. በመካከላችሁ ሳለሁ ኢየሱስ ክርስቶስን ያውም የተሰቀለውን፣ እርሱን ብቻ እንጂ ሌላ እንዳላውቅ ወስኜ ነበርና።

3. ወደ እናንተ የመጣሁት በድካምና በፍርሀት፣ እንዲሁም በብዙ መንቀጥቀጥ ነበር።

4. ቃሌም ስብከቴም የመንፈስን ኀይል በመግለጥ እንጂ፣ በሚያባ ባል የጥበብ ቃል አልነበረም፤

5. ይኸውም እምነታችሁ በእግዚአብሔር ኀይል እንጂ በሰው ጥበብ ላይ እንዳይመሠረት ነው።

6. በበሰሉ ሰዎች መካከል ግን ጥበብን እንናገራለን፤ ይሁን እንጂ የዚችን ዓለም ጥበብ ወይም የሚጠፉትን የዚችን ዓለም ገዦች ጥበብ አይደለም።

7. ነገር ግን ተሰውሮ የነበረውን የእግዚአብሔርን ምስጢር ጥበብ ነው፤ ይህም ጥበብ እግዚአብሔር ከዘመናት በፊት ለክብራችን አስቀድሞ የወሰነው ነው።

8. ከዚህ ዓለም ገዦች አንዳቸውም ይህን ጥበብ አልተረዱትም፤ ቢረዱትማ ኖሮ የክብርን ጌታ ባልሰቀሉት ነበር።

9. ይሁን እንጂ፣ እንደ ተጻፈው፣“ዐይን ያላየውን፣ጆሮ ያልሰማውን፣የሰውም ልብ ያላሰበውን፣እግዚአብሔር ለሚወዱት አዘጋጅቶአል፤”

10. እግዚአብሔር ግን ይህን በመንፈሱ አማካይነት ለእኛ ገልጦልናል።መንፈስም የእግዚአብሔርን ጥልቅ ነገር እንኳ ሳይቀር ሁሉን ይመረምራል።

11. በውስጡ ካለው ከራሱ መንፈስ በስተቀር ከሰው መካከል የአንድን ሰው ሐሳብ የሚያውቅ ማን አለ? እንደዚሁም ከእግዚአብሔር መንፈስ በስተቀር፣ የእግዚአብሔርን ሐሳብ የሚያውቅ ማንም የለም።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 1 ቆሮንቶስ 2