ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘፍጥረት 48:10-22 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

10. በዚህ ጊዜ እስራኤል ዐይኖቹ በእርጅና ምክንያት በመድከማቸው አጥርቶ ማየት ይሳነው ነበር፤ ስለዚህ ዮሴፍ ልጆቹን አባቱ ዘንድ አቀረባቸው፤ አባቱም ስሞ ዐቀፋቸው።

11. እስራኤልም ዮሴፍን፣ “ዐይንህን እንደ ገና ዐያለሁ ብዬ አላሰብኩም ነበር፤ እግዚአብሔር (ኤሎሂም) ግን ልጆችህን ጭምር ለማየት አበቃኝ” አለው።

12. ዮሴፍም ልጆቹን ከእስራኤል ጒልበት ፈቀቅ በማድረግ አጐንብሶ በግንባሩ መሬት ላይ ተደፋ።

13. ከዚያም ዮሴፍ ሁለቱን ልጆቹን ይዞ ኤፍሬምን ከራሱ በስተ ቀኝ፣ ከእስራኤል በስተ ግራ፣ ምናሴን ደግሞ ከራሱ በስተ ግራ፣ ከእስራኤል በስተ ቀኝ በኩል አቀረባቸው።

14. እስራኤል ግን ቀኝ እጁን በታናሹ በኤፍሬም ራስ ላይ አኖረ፤ ግራ እጁንም በቀኝ እጁ ላይ አስተላልፎ በበኵሩ በምናሴ ራስ ላይ አኖረ።

15. ከዚህ በኋላ ዮሴፍን ባረከ፤ እንዲህም አለው፤“አባቶቼ አብርሃምና ይስሐቅ በፊቱየተመላለሱት እግዚአብሔር (ኤሎሂም)፣ለእኔም እስከ ዛሬ ድረስበዘመኔ ሁሉ እረኛ የሆነኝ አምላክ (ኤሎሂም)፣

16. ከጒዳትም ሁሉ የታደገኝ መልአክ፣እርሱ እነዚህን ልጆች ይባርክ፤እነርሱም በስሜ፣በአባቶቼ በአብርሃምናበይስሐቅ ስም ይጠሩ፤በምድር ላይ እጅግ ይብዙ።

17. ዮሴፍ፣ አባቱ ቀኝ እጁን በኤፍሬም ራስ ላይ ማድረጉን ሲያይ ተከፋ፤ ከኤፍሬም ራስ ላይ አንሥቶ በምናሴ ራስ ላይ ለማኖር የአባቱን እጅ ያዘ፤

18. ዮሴፍም፣ “አባቴ ሆይ፤ እንዲህ አይደለም በኵሩ ይህኛው ስለ ሆነ፣ ቀኝ እጅህን እርሱ ራስ ላይ አድርግ” አለው።

19. አባቱ ግን፣ “ዐውቃለሁ፤ ልጄ ዐውቃለሁ፤ እርሱም እኮ ሕዝብ ይሆናል፤ ታላቅም ይሆናል፤ ይሁን እንጂ ታናሽ ወንድሙ ከእርሱ ይበልጣል፤ ዘሮቹም ታላቅ ሕዝቦች ይሆናሉ” ብሎ እምቢ አለው።

20. በዚያን ዕለት ባረካቸው፤ እንዲህም አላቸው፤“በአንተ ስም እስራኤል እንዲህ ብሎ ይመርቃል፤“እግዚአብሔር (ኤሎሂም) እንደ ኤፍሬምና እንደ ምናሴ ያድርጋችሁ።”በዚህ ሁኔታም ኤፍሬምን ከምናሴ አስቀደመው።

21. ከዚህ በኋላ እስራኤል ዮሴፍን እንዲህ አለው፤ እኔ የምሞትበት ጊዜ ተቃርቦአል፤ ነገር ግን እግዚአብሔር (ኤሎሂም) ከእናንተ ጋር ይሆናል፤ ወደ አባቶቻችሁም ምድር መልሶ ያገባችኋል።

22. እነሆ በሰይፌና በቀስቴ ከአሞራውያን እጅ የወሰድኳትን ዐምባ ከወንድሞችህ ድርሻ አብልጬ ለአንተ ሰጥቼሃለሁ።”

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘፍጥረት 48