ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘፍጥረት 24:28-44 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

28. ልጂቷ ሮጣ ሄዳ፣ የሆነውን ሁሉ ለእናቷ ቤተ ሰቦች ነገረች።

29. ርብቃም ላባ የተባለ ወንድም ነበራት፤ እርሱም ሰውየው ወዳለበት የውሃ ጒድጓድ ፈጥኖ ሄደ።

30. እኅቱ ያደረገችውን የወርቅ ቀለበትና አምባሮች እንዳየ፣ እንዲሁም ርብቃ ሰውየው ያላትን ስትናገር እንደ ሰማ፣ ወዲያውኑ ወደ ሰውየው ሄደ፤ በምንጩም ዳር ከግመሎቹ አጠገብ ቆሞ አገኘው፤

31. እርሱንም “አንተ የእግዚአብሔር (ያህዌ) ቡሩክ ሆይ፤ ና፤ እዚህ ውጭ የቆምኸው ለምንድን ነው? እነሆ፤ ለአንተ ማረፊያ ለግመሎችህም ማደሪያ አዘጋጅቻለሁ” አለው።

32. ሰውየው ከላባ ጋር ወደ ቤት ሄደ፤ የግመሎቹ ጭነት ተራግፎ ገለባና ድርቈሽ ተሰጣቸው፤ ለእርሱና አብረውት ለነበሩት ሰዎች የእግር ውሃ ቀረበላቸው።

33. ለሰውየውም ማዕድ ቀረበለት፤ እርሱ ግን፣ “የመጣሁበትን ጒዳይ ሳልናገር እህል አልቀምስም” አለ።ላባም፣ “እሺ፤ ተናገር” አለው።

34. እርሱም እንዲህ አለ፤ “እኔ የአብርሃም አገልጋይ ነኝ፤

35. እግዚአብሔር (ያህዌ) ጌታዬን እጅግ ባርኮታል፤ እርሱም በልጽጓል፤ በጎችና ከብቶች፣ ብርና ወርቅ፣ ወንድና ሴት አገልጋዮች፣ ግመሎችና አህዮች ሰጥቶታል።

36. የጌታዬ ሚስት ሣራ በስተርጅናዋ ወንድ ልጅ ወልዳለታለች፤ ጌታዬም ያለውን ሀብት ሁሉ ለልጁ ሰጥቶታል።

37. ጌታዬ እንዲህ ሲል አማለኝ፤ ‘ከዚህ ከምኖርበት አገር፣ ከከነዓናውያን ሴቶች ልጆች ጋር ልጄን አታጋባው፤

38. ነገር ግን ወደ አባቴ ቤት፣ ወደ ገዛ ወገኖቼ ሄደህ ለልጄ ሚስት አምጣለት’።

39. “እኔም ጌታዬን፣ ‘ሴቲቱ ከእኔ ጋር ወደዚህ ለመምጣት ባትፈቅድስ?’ ብዬ ጠየቅሁት።

40. “እርሱም እንዲህ አለኝ፤ ‘አካሄዴን በፊቱ ያደረግሁ እግዚአብሔር (ያህዌ) መልአኩን ከአንተ ጋር ይልካል፤ ከገዛ ወገኖቼና ከአባቴ ቤት፣ ለልጄ ሚስት እንድታመጣለት መንገድህን ያቃናል።

41. ወደ ወገኖቼ ከሄድህ፣ ከመሐላው የተፈታህ ትሆናለህ፤ እነርሱ እንኳ ልጂቱን አንሰጥም ቢሉህ፣ ከመሐላው ንጹሕ ትሆናለህ’ አለኝ።

42. “እኔም ዛሬ ወደ ውሃው ጒድጓድ ስደርስ እንዲህ ብዬ ጸለይሁ፤ ‘የጌታዬ የአብርሃም አምላክ እግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) ሆይ፤ ፈቃድህ ቢሆን የመጣሁበትን ጒዳይ አቃናልኝ፤

43. እነሆ፤ በምንጩ አጠገብ ቆሜአለሁ፤ ውሃ ልትቀዳ የምትመጣውን ኮረዳ፣ “ከእንስራሽ ውሃ አጠጪኝ” ስላት፣

44. እሺ ጠጣ፤ ለግመሎችህም እቀዳላቸዋለሁ” የምትለኝ እርሷ እግዚአብሔር (ያህዌ) ለጌታዬ ልጅ የመረጣት ትሁን።’

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘፍጥረት 24