ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12
  13. 13
  14. 14
  15. 15
  16. 16
  17. 17
  18. 18
  19. 19
  20. 20
  21. 21
  22. 22
  23. 23
  24. 24
  25. 25
  26. 26
  27. 27
  28. 28
  29. 29
  30. 30
  31. 31
  32. 32
  33. 33
  34. 34
  35. 35
  36. 36
  37. 37
  38. 38
  39. 39
  40. 40
  41. 41
  42. 42
  43. 43
  44. 44
  45. 45
  46. 46
  47. 47
  48. 48
  49. 49
  50. 50

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘፍጥረት 18 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

ሦስቱ እንግዶች

1. ቀትር ላይ አብርሃም በመምሬ ትልልቅ ዛፎች አቅራቢያ በምትገኘው ድንኳኑ ደጃፍ ተቀምጦ ሳለ እግዚአብሔር (ያህዌ) ተገለጠለት፤

2. ቀና ብሎም ሲመለከት፣ ሦስት ሰዎች ቆመው አየ፤ ወዲያውም ከድንኳኑ ደጃፍ ተነሥቶ፣ ፈጥኖ ወደ ሰዎቹ ሄደ፤ ወደ መሬት ዝቅ ብሎም እጅ ነሣ።

3. አብርሃምም እንዲህ አለ፤ “ጌታዬ፤ በፊትህ ሞገስ አግኝቼ እንደሆነ፣ ባሪያህን አልፈህ አትሂድ፤

4. ጥቂት ውሃ ይምጣላችሁና እግራችሁን ታጠቡ፤ እዚህም ከዛፉ ሥር ዐረፍ በሉ።

5. ወደ እኔ ወደ አገልጋያችሁ ከመጣችሁ፣ እህል ቀምሳችሁ ትበረቱ ዘንድ ምግብ ላቅርብላችሁና ጒዞአችሁን ትቀጥላላችሁ።”እነርሱም፣ “መልካም፤ እንዳልኸው አድርግ” አሉት።

6. አብርሃም በፍጥነት ሣራ ወዳለችበት ወደ ድንኳኑ ገብቶ፣ “ቶሎ ብለሽ ሦስት መስፈሪያ ስልቅ ዱቄት አቡኪና ቂጣ ጋግሪ” አላት።

7. ከዚያም ወደ መንጋው በጥድፊያ ሄዶ፣ አንድ ፍርጥም ያለ ሥጋው ገር የሆነ ጥጃ መርጦ ለአገልጋዩ ሰጠው፤ አገልጋዩም ጥጃውን ዐርዶ አዘጋጀው።

8. አብርሃምም እርጎ፣ ወተትና የተዘጋጀውን የጥጃ ሥጋ አቀረበላቸው፤ ሲበሉም ዛፉሥር አጠገባቸው ቆሞ ነበር።

9. እነርሱም አብርሃምን፣ “ሚስትህ ሣራ የት አለች?” ብለው ጠየቁት።እርሱም፣ “ድንኳን ውስጥ ናት” አላቸው።

10. እግዚአብሔርም (ያህዌ)፣ “የዛሬ ዓመት በዚሁ ጊዜ በእርግጥ ተመልሼ እመጣለሁ፤ ሚስትህ ሣራ ወንድ ልጅ ትወልዳለች” አለው።ሣራም በዚህ ጊዜ ከበስተ ጀርባው ካለው ከድንኳኑ ደጃፍ ሆና ትሰማ ነበር።

11. በዚያን ጊዜ አብርሃምና ሣራ አርጅተው፣ ዕድሜአቸው ገፍቶ ነበር፤ ሣራም ልጅ የመውለጃዋ ዕድሜ ዐልፎ ነበር።

12. ሣራ በልቧ፣ “ካረጀሁና ጌታዬም ከደከመ በኋላ በዚህ ነገር መደሰት ይሆንልኛል?” ብላ ሣቀች።

13. እግዚአብሔርም (ያህዌ) አብርሃምን እንዲህ አለው፤ “ሣራ፣ ‘ካረጀሁ በኋላ ልጅ እንዴት አድርጌ እወልዳለሁ’ ስትል ለምን ሣቀች?

14. ለእግዚአብሔር (ያህዌ) የሚሳነው ነገር አለን? የዛሬ ዓመት በተባለው ጊዜ ተመልሼ እመጣለሁ፤ ሣራም ልጅ ይኖራታል።”

15. ሣራ ስለ ፈራች፣ “ኧረ አልሣቅሁም” ብላ ዋሸች።እርሱ ግን፣ “ሣቅሽ እንጂ” አላት።

አብርሃም ስለ ሰዶም ማለደ

16. ሰዎቹም ለመሄድ ሲነሡ፣ ቊልቊል ወደ ሰዶም ተመለከቱ፤ አብርሃምም ሊሸኛቸው አብሮአቸው ወጣ።

17. እግዚአብሔርም (ያህዌ) እንዲህ አለ፤ “እኔ የማደርገውን ነገር ከአብርሃም እሰውራለሁን?

18. አብርሃም በእውነት ታላቅና ብርቱ ሕዝብ ይሆናል፤ የምድር ሕዝቦችም ሁሉ በእርሱ ይባረካሉ።

19. ትክክለኛና ቀና የሆነውን በማድረግ የእግዚአብሔርን (ያህዌ) መንገድ ይጠብቁ ዘንድ ልጆቹንና ከእርሱ በኋላ ቤተ ሰቦቹን እንዲያዝ መርጬዋለሁ፤ ይኸውም እግዚአብሔር (ያህዌ) ለአብርሃም የሰጠው ተስፋ ሁሉ እንዲፈጸም ነው።”

20. ደግሞም እግዚአብሔር (ያህዌ) እንዲህ አለ፤ “በሰዶምና በገሞራ ላይ የሚሰማው ጩኸት እጅግ በዝቶአል፤ ኀጢአታቸውም እጅግ ከፍቶአል፤

21. አድራጎታቸው እኔ ዘንድ እንደ ደረሰው ጩኸት መሆኑን ለማየት ወደዚያው እወርዳለሁ፤ እንደዚያ ካልሆነም ዐውቃለሁ።”

22. ሰዎቹም ፊታቸውን ወደ ሰዶም አቅንተው ሄዱ፤ አብርሃም ግን በእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት እንደ ቆመ ነበር።

23. አብርሃምም ወደ እርሱ ቀረብ ብሎ እንዲህ አለ፤ “በእርግጥ ጻድቁን ከኀጢአተኛው ጋር አብረህ ታጠፋለህን?

24. አምሳ ጻድቃን በከተማዪቱ ቢገኙ፣ በውኑ ነዋሪዎቹን ሁሉ ታጠፋለህን? በውስጧ ለሚገኙ አምሳ ጻድቃን ስትል ከተማዪቱን አትምርምን?

25. እንዲህስ አይሁን፤ ጻድቁን ከኀጢአተኛው ጋር እንዴት ትገድለዋለህ? ይህን የመሰለው አድራጎት ከአንተ ይራቅ፤ የምድር ሁሉ ዳኛ በቅን አይፈርድምን?”

26. እግዚአብሔርም (ያህዌ)፣ “በሰዶም ከተማ አምሳ ጻድቃን ባገኝ ለእነርሱ ስል አገሪቱን በሞላ እምራለሁ” አለ።

27. ደግሞም አብርሃም እንዲህ አለ፤ “እኔ ከንቱ፣ ትቢያና ዐመድ ሆኜ ሳለሁ ከጌታ (አዶናይ) ጋር ለመናገር አንዴ ደፍሬአለሁ፤

28. ለመሆኑ ከአምሳው ጻድቃን አምስት ቢጐድሉ በአምስቱ ሰዎች ምክንያት መላ ከተማዋን ታጠፋለህን?”እርሱም፣ “አርባ አምስት ጻድቃን ባገኝ አላጠፋትም” አለ።

29. አብርሃምም እንደ ገና፣ “ምናልባት አርባ ጻድቃን ቢገኙስ?” አለ እርሱም፣ “ለአርባው ስል እምራታለሁ” አለ።

30. ደግሞም አብርሃም፣ “ጌታዬ (አዶናይ) አይቈጣ፤ እባክህ ልናገር፤ ሠላሳ ጻድቃን ብቻ ቢገኙስ?”እርሱም፣ “ሠላሳ ባገኝ አላጠፋትም” ብሎ መለሰ።

31. አብርሃምም፣ “ከጌታ (አዶናይ) ጋር እናገር ዘንድ መቼም አንዴ ደፍሬአለሁና ምናልባት ሃያ ብቻ ቢገኙስ?” አለ።እርሱም፣ “ሃያ ቢገኙ፣ ለእነርሱ ስል እምራታለሁ” አለ።

32. አብርሃምም፣ “ጌታዬ (አዶናይ) አይቈጣ፤ አንድ ጊዜ ብቻ ልናገር፤ ምናልባት ዐሥር ብቻ ቢገኙስ?” አለ።እርሱም “ስለ ዐሥሩ ስል አላጠፋትም” ብሎ መለሰ።

33. እግዚአብሔር (ያህዌ) ከአብርሃም ጋር ንግግሩን ከጨረሰ በኋላ ሄደ፤ አብርሃምም ወደ ቤቱ ተመለሰ።