ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘፀአት 4:1-9 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. ሙሴም “ባያምኑኝስ፤ ቃሌን ባይቀበሉስ፤ ‘እግዚአብሔር (ያህዌ) አልተገለጠልህም’ ቢሉኝስ?” ብሎ መለሰ።

2. እግዚአብሔርም (ያህዌ)፣ “በእጅህ የያዝሀት እርሷ ምንድን ናት?” ሲል ጠየቀው፤ እርሱም መልሶ፣ “በትር ናት” አለው።

3. እግዚአብሔርም (ያህዌ)፣ “መሬት ላይ ጣላት” አለው።ሙሴ በትሩን መሬት ላይ ጣላት፤ እባብም ሆነች፤ ከአጠገቧም ሸሸ።

4. እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን፣ “በል እጅህን ዘርጋና ጅራቷን ያዛት” አለው። ሙሴም እጁን ዘርግቶ ሲይዛት እባቧ ተለውጣ በእጁ ላይ እንደ ገና በትር ሆነች።

5. እግዚአብሔርም (ያህዌ) “ይህ የሆነው የአባቶቻቸው አምላክ፣ የአብርሃም አምላክ፣ የይስሐቅ አምላክ፣ የያዕቆብ አምላክ እግዚአብሔር (ያህዌ) የተገለጠልህ መሆኑን እንዲያምኑ ነው” አለው።

6. እግዚአብሔርም (ያህዌ) ደግሞ፣ “እጅህን ብብትህ ውስጥ አስገባ” አለው። ሙሴም እጁን ብብቱ ውስጥ አስገባ፤ ከብብቱ ውስጥ ባወጣት ጊዜ እጁ እንደ በረዶ ለምጽ ሆነች።

7. “አሁንም ደግሞ እጅህን ወደ ብብትህ መልሰህ አስገባ” አለው። ሙሴም እጁን መልሶ ብብቱ ውስጥ አስገባ፤ እንደ ገና እጁን ከብብቱ ውስጥ ባወጣት ጊዜ፣ ተመልሳ እንደ ሌላው የሰውነቱ ክፍል ሆነች።

8. እግዚአብሔርም (ያህዌ)፣ “እንግዲህ ባያምኑህ ወይም የመጀመሪያውን ታምራዊ ምልክት ባይቀበሉ እንኳ ሁለተኛውን ያምናሉ።

9. እነዚህን ሁለት ምልክቶች ባያምኑ ወይም ቃልህን ባይቀበሉ ግን፣ ከአባይ ወንዝ ጥቂት ውሃ ቀድተህ በደረቅ ምድር ላይ አፍስሰው። ከወንዙም ቀድተህ ያፈሰስኸው ውሃ በምድር ላይ ደም ይሆናል።”

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘፀአት 4