ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12
  13. 13
  14. 14
  15. 15
  16. 16
  17. 17
  18. 18
  19. 19
  20. 20
  21. 21
  22. 22
  23. 23
  24. 24
  25. 25
  26. 26
  27. 27
  28. 28
  29. 29
  30. 30
  31. 31
  32. 32
  33. 33
  34. 34
  35. 35
  36. 36
  37. 37
  38. 38
  39. 39
  40. 40

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘፀአት 29 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

የካህናት መቀደስ

1. “ካህናት ሆነው እንዲያገለግሉኝ ትቀድሳቸው ዘንድ የምታደርገው ይህ ነው፤ ነውር የሌለባቸው አንድ ወይፈንና ሁለት አውራ በጎች ውሰድ፤

2. እርሾ ከሌለው ከምርጥ የስንዴ ዱቄት ቂጣ፣ በዘይት የተለወሰ የቂጣ እንጎቻና በዘይት የተቀባ ኅብስት ጋግር።

3. በሌማት ላይ አድርገህ ከወይፈኑና ከሁለቱ አውራ በጎች ጋር አቅርባቸው።

4. ከዚያም አሮንና ወንድ ልጆቹን ወደ መገናኛው ድንኳን ደጃፍ በማምጣት በውሃ እጠባቸው።

5. ልብሶቹን ወስደህ ለአሮን አልብሰው፤ ሸሚዝ፣ የኤፉድ ቀሚስ፣ ኤፉዱንና የደረት ኪሱን አልብሰው፤ ኤፉዱን በእርሱ ላይ በጥበብ በተሠራ መታጠቂያ እሠረው።

6. መጠምጠሚያውን በራሱ ላይ በማድረግ የተቀደሰውን አክሊል ከመጠምጠሚያው ጋር አያይዘው።

7. ቅብዐ ዘይት ወስደህ በራሱ ላይ በማፍሰስ ቅባው።

8. ወንዶች ልጆቹን አምጥተህ ሸሚዞች አልብሳቸው።

9. የራስ ማሰሪያዎችንም አድርግላቸው፤ ከዚያም አሮንንና ወንዶች ልጆቹን መታጠቂያዎችን አስታጥቃቸው፤ ክህነት የዘላለም ሥርዐት ይሆንላቸዋል፤ በዚህም መንገድ አሮንንና ወንዶች ልጆቹን ትክናቸዋለህ።

10. “ወይፈኑን በመገናኛው ድንኳን ፊት ለፊት በማምጣት አሮንና ወንዶች ልጆቹ በራሱ ላይ እጆቻቸውን ይጫኑበት።

11. በመገናኛው ድንኳን ደጃፍ ላይ በእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት እረደው።

12. ከወይፈኑ ደም ወስደህ በመሠዊያው ቀንዶች ላይ በጣቶችህ አድርግበት፤ የቀረውንም ከመሠዊያው ሥር አፍሰው።

13. ከዚያም በሆድ ዕቃዎች ያለውን ስብ ሁሉ፣ የጉበቱን መሸፈኛና ሁለቱንም ኵላሊቶች በዙሪያቸው ካለው ስብ ጋር ወስደህ በመሠዊያው ላይ አቃጥላቸው።

14. ነገር ግን የወይፈኑን ሥጋ፣ ቆዳውንና የማይበላውን አሰስ ገሠስ ሥጋ ከሰፈር ውጭ አቃጥለው፤ የኀጢአት መሥዋዕት ነው።

15. “ከሁለቱ አውራ በጎች አንዱን ወስደህ፣ አሮንና ወንዶች ልጆቹ በራሱ ላይ እጃቸውን ይጭኑበታል።

16. አውራውንም በግ እረደው፤ ደሙንም ወስደህ በመሠዊያው ላይ ዙሪያውን እርጨው።

17. አውራ በጉን በየብልቱ ቈራርጠህ፣ የሆድ ዕቃውንና እግሮቹን አጥበህ ከራሱና ከሌሎቹ ቁርጥራጭ ብልቶች ጋር አኑረው።

18. ከዚያም አውራ በጉን በሙሉ በመሠዊያው ላይ አቃጥለው፤ ለእግዚአብሔር (ያህዌ) የሚቃጠል መሥዋዕት ጣፋጭ መዓዛና ለእግዚአብሔር (ያህዌ) በእሳት የሚቀርብ መሥዋዕት ነው።

19. “ሌላውን አውራ በግ ወስደህ አሮንና ወንዶች ልጆቹ በራሱ ላይ እጆቻቸውን ይጭኑበታል።

20. አውራውንም በግ እረደው፤ ከደሙም ወስደህ የአሮንንና የወንዶች ልጆቹን የቀኝ ጆሮዎቻቸውን ጫፍ የቀኝ እጆቻቸውን አውራ ጣቶች፣ የቀኝ እግራቸውንም አውራ ጣቶች ቅባቸው፤ ከዚያም ደሙን በመሠዊያው ላይ ዙሪያውን እርጨው።

21. በመሠዊያው ላይ ካለው ደምና ከቅብዐ ዘይቱ ወስደህ በአሮንና በልብሶቹ ላይ እንዲሁም በወንዶች ልጆቹና በልብሶቻቸው ላይ እርጨው። ከዚያም እርሱና ወንዶች ልጆቹ እንዲሁም ልብሶቻቸው የተቀደሱ ይሆናሉ።

22. ‘ከዚህ አውራ በግ ስቡን፣ ላቱን፣ በሆድ ዕቃው ውስጥ ያለውን ስብ፣ የጉበቱን ሽፋን፣ ሁለቱን ኵላሊቶችና በዙሪያቸው ያለውን ስብና ቀኙን ወርች ውሰድ፤ ይህ የክህነት አውራ በግ ነው።

23. በእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት በሌማት ካለው ያለ እርሾ ከተጋገረው ቂጣ፣ ዳቦ፣ በዘይት የተሠራ እንጎቻና ኅብስት ውሰድ።

24. እነዚህን ሁሉ በአሮንና በወንዶች ልጆቹ እጆች ላይ በማኖር እንደሚወዘወዝ መሥዋዕት በእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት ወዝውዛቸው።

25. ከዚያም ከእጃቸው ወስደህ ከሚቃጠለው መሥዋዕት ጋር ለእግዚአብሔር (ያህዌ) መልካም መዓዛ እንዲሆን በመሠዊያው ላይ አቃጥለው፤ ይህም ለእግዚአብሔር (ያህዌ) በእሳት የሚቃጠል መሥዋዕት ነው።

26. ለአሮን ክህነት የአውራ በጉን ፍርምባ ከወሰድህ በኋላ እንደሚወዘወዝ መሥዋዕት በእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት ወዝውዘው ይህም የአንተ ድርሻ ይሆናል።

27. “ለአሮንና ለወንዶች ልጆቹ ለክህነት የሆኑትን የአውራውን በግ ብልቶች፣ ቀድሳቸው። የተወዘወዘውን ፍርምባና የቀረበውን ወርች

28. ለአሮንና ለወንዶች ልጆቹ የዘወትር የእስራኤላውያን ድርሻ የሚሆነው ይህ ነው፤ ከኅብረት መሥዋዕታቸው እስራኤላውያን ለእግዚአብሔር (ያህዌ) የሚያቀርቡት ነው።

29. “የአሮን የተቀደሱ ልብሶች ለትውልዶቹ ይሆናሉ፤ ይኸውም በእነርሱ ይቀቡና ክህነትን ይቀበሉ ዘንድ ነው።

30. ካህን በመሆን እርሱን የሚተካውና በመቅደሱ ለማገልገል ወደ መገናኛው ድንኳን የሚመጣው ወንድ ልጅ ሰባት ቀን ይለብሳቸዋል።

31. “የክህነቱን አውራ በግ ወስደህ ሥጋውን በተቀደሰ ስፍራ ቀቅለው።

32. አሮንና ወንዶች ልጆቹ በመገናኛው ድንኳን ደጃፍ ላይ የአውራውን በግ ሥጋና በሌማት ያለውን ዳቦ ይብሉ።

33. ለክህነታቸውና ለመቀደሳቸው ማስተስረያ የሆኑትን እነዚህን መሥዋዕቶችን ይብሉ፤ የተቀደሱ ስለሆኑ ሌላ ማንም አይብላቸው።

34. ከክህነቱ የአውራ በግ ሥጋ ወይም ከቂጣው እስከ ንጋት ድረስ ቢተርፍ አቃጥለው፤ የተቀደሰ ስለ ሆነ መበላት የለበትም።

35. “ክህነታቸውን በሰባት ቀን በመፈጸም ለአሮንና ለወንዶች ልጆቹ ያዘዝሁህን ሁሉ አድርግላቸው።

36. ለማስተስረያ የሚሆን አንድ ወይፈን የኀጢአት መሥዋዕት አድርገህ በየዕለቱ ሠዋ፤ ለመሠዊያውም ማስተስረያ በማቅረብ መሠዊያውን አንጻው፤ ትቀድሰውም ዘንድ ቅባው።

37. ለሰባት ቀን ለመሠዊያው ማስተስረያ በማድረግ ቀድሰው፤ ከዚያም መሠዊያው እጅግ የተቀደሰ ይሆናል፤ የሚነካውም ሁሉ የተቀደሰ ይሆናል።

38. “በየዕለቱ ያለ ማቋረጥ በመሠዊያው ላይ የምታቀርበው ይህ ነው፤ ዓመት የሞላቸው ሁለት የበግ ጠቦቶች፤

39. አንዱን በማለዳ፣ ሌላውን በምሽት አቅርብ።

40. ከመጀመሪያው የበግ ጠቦት ጋር የኢፍ መስፈሪያ አንድ ዐሥረኛ ምርጥ ዱቄትን ተወቅጦ ከተጠለለ ሩብ ኢፍ ዘይት ጋር ለውስና ሩብ ኢን ወይንን ደግሞ የመጠጥ መሥዋዕት በማድረግ አቅርብ።

41. ሌላውን የበግ ጠቦት በማለዳው እንደ ቀረበው ተመሳሳይ ከሆነው የእህልና የመጠጥ መሥዋዕት ጋር በምሽት ሠዋው፤ ይህም ጣፋጭ መዓዛና ለእግዚአብሔር (ያህዌ) በእሳት የሚቀርብ መሥዋዕት ነው።

42. “ይህ የሚቃጠል መሥዋዕት በእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት በመገናኛው ድንኳን ደጃፍ ላይ በሚመጡት ትውልዶች ዘወትር ይደረጋል፤ በዚያ እገናኝሃለሁ፤ እናገርሃለሁም፤

43. በዚያ ደግሞ ከእስራኤላውያን ጋር እገናኛለሁ፤ ስፍራውም በክብሬ ይቀደሳል።

44. “ስለዚህ የመገናኛው ድንኳንና መሠዊያውን እኔ እቀድሳለሁ፤ ካህናት ሆነው እንዲያገለግሉኝ አሮንና ወንድ ልጆቹን እቀድሳለሁ።

45. ከዚያም በእስራኤላውያን መካከል እኖራለሁ፤ አምላካቸውም (ኤሎሂም) እሆናለሁ።

46. በመካከላቸውም እኖር ዘንድ ከግብፅ ያወጣኋቸው እኔ አምላካቸው እግዚአብሔር (ያህዌ) መሆኔን ያውቃሉ፤ እኔ እግዚአብሔር (ያህዌ) አምላካቸው ነኝ።