ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘፀአት 18:19-27 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

19. ምክር እሰጥሃለሁና አሁን እኔን አድምጠኝ፤ እግዚአብሔር (ኤሎሂም) ከአንተ ጋር ይሁን። አንተ በእግዚአብሔር (ኤሎሂም) ፊት (የሕዝብ ተወካይ መሆን አለብህ)፤ ክርክራቸውን ወደ እርሱ ታቀርባለህ።

20. ሥርዐቶቹንና ሕጎቹን አስተምራቸው፤ እንዴት መኖር እንዳለባቸውና ምን መሥራት እንደሚገባቸው አሳያቸው።

21. ነገር ግን ችሎታ ያላቸውን ሰዎች ከሕዝቡ ሁሉ ምረጥ፤ እነዚህም ሰዎች እግዚአብሔርን (ኤሎሂም) የሚፈሩ፣ ታማኞችና በማታለል የሚገኘውን ጥቅም የሚጸየፉ ይሁኑ። የሺህ፣ የመቶ፣ የአምሳ፣ የዐሥር፣ አለቃ አድርገህ ሹማቸው።

22. በማንኛውም ጊዜ ሕዝቡን ይዳኙ፤ ቀላሉን ነገር እነርሱ ይወስኑ፤ አስቸጋሪ የሆነውን ጒዳይ ሁሉ ግን ለአንተ እንዲያቀርቡ አድርግ፤ ሥራውን ስለሚያግዙህ ሸክምህ ይቃለላል።

23. አንተ ይህን ብታደርግና እግዚአብሔርም (ኤሎሂም) ይህንኑ ቢያዝህ፣ ድካምህን መቋቋም ትችላለህ፤ እነዚህም ሰዎች ሁሉ ረክተው ወደ ቤታቸው ይሄዳሉ።

24. ሙሴ አማቱን ሰማ፤ ያለውንም ሁሉ ፈጸመ።

25. ከእስራኤል መካከል ችሎታ ያላቸውን ሰዎች መረጠና፤ የሕዝብ መሪዎች፣ በሺዎች፣ በመቶዎች፣ በአምሳዎች በዐሥሮች ላይም አለቆች አደረጋቸው።

26. ሁልጊዜም የሕዝብ ዳኞች ሆነው አገለገሉ፤ አስቸጋሪ ጉዳዮችን ወደ ሙሴ አመጡ፤ ቀላል የሆነውን ራሳቸው ወሰኑ።

27. ከዚያም ሙሴ አማቱን በጒዞው ሸኘው፤ ዮቶርም ወደ አገሩ ተመለሰ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘፀአት 18