ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12
  13. 13
  14. 14
  15. 15
  16. 16
  17. 17
  18. 18
  19. 19
  20. 20
  21. 21
  22. 22
  23. 23
  24. 24
  25. 25
  26. 26
  27. 27
  28. 28
  29. 29
  30. 30
  31. 31
  32. 32
  33. 33
  34. 34

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘዳግም 9 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

የሕዝቡ አለመታዘዝ

1. እስራኤል ሆይ፣ ስማ፤ ሰማይ ጠቀስ ቅጥር ያላቸው ታላላቅ ከተሞች ያሏቸውን፣ ከአንተ ይልቅ ታላቅና ብርቱ የሆኑትን አሕዛብ አስለቅቀህ ለመግባት ዮርዳኖስን አሁን ትሻገራለህ።

2. ዔናቃውያን ብርቱና ቁመተ ረጃጅም ሕዝቦች ናቸው፤ ስለ እነርሱ ታውቃለህ፤ “ዔናቃውያንን ማን ሊቋቋማቸው ይችላል?” ሲባልም ሰምተሃል።

3. ይሁን እንጂ እንደሚባላ እሳት ከፊትህ ቀድሞ የሚሻገረው አምላክህእግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) መሆኑን ዛሬ እርግጠኛ ሁን፤ እነርሱን ያጠፋቸዋል፤ በፊትህም ድል ያደርጋቸዋል፤ አንተም እግዚአብሔር (ያህዌ) በሰጠህ ተስፋ መሠረት ታስወጣቸዋለህ፤ በፍጥነትም ትደመስሳቸዋለህ።

4. አምላክህእግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) እነርሱን ከፊትህ ካስወጣቸው በኋላ፣ “ይህችን ምድር እንድወርስ እግዚአብሔር (ያህዌ) ወደዚህ ያመጣኝ፣ ከጽድቄ የተነሣ ነው” ብለህ በልብህ አታስብ። በዚህ አይደለም፤ እነዚህን አሕዛብ እግዚአብሔር (ያህዌ) ከፊትህ የሚያሳድዳቸው በክፋታቸው ምክንያት ነው።

5. ምድራቸውን ገብተህ የምትወርሳት ከጽድቅህ ወይም ከልብህ ቅንነት የተነሣ ሳይሆን፣ ለአባቶችህ ለአብርሃም፣ ለይስሐቅና ለያዕቆብ የማለላቸውን ቃል ለመፈጸም አምላክህ እግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) እነዚህን አሕዛብ ከክፋታቸው የተነሣ ከፊትህ ስለሚያባርራቸው ነው።

6. ስለዚህ አምላክህ እግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) ይህችን መልካም ምድር እንድትወርሳት የሚሰጥህ ከጽድቅህ የተነሣ አለመሆኑን አስተውል፤ አንተ ዐንገተ ደንዳና ነህና።

የወርቁ ጥጃ

7. አምላክህን እግዚአብሔርን (ኤሎሂም ያህዌ) በምድረ በዳ እንዴት እንዳስቈጣኸው አስታውስ፤ ከቶም አትርሳ። ከግብፅ ከወጣህበት ዕለት አንሥቶ እዚህ ቦታ እስከ ደረስህበት ጊዜ በእግዚአብሔር (ያህዌ) ላይ እንዳመፅህ ነህ።

8. በኮሬብ እግዚአብሔርን (ያህዌ) ለቊጣ አነሣሣችሁት፤ እርሱም እናንተን ሊያጠፋችሁ እጅግ ተቈጣ።

9. እኔም የድንጋይ ጽላቶቹን፣ እግዚአብሔር (ያህዌ) ከእናንተ ጋር የገባውን የኪዳን ጽላቶች ለመቀበል ወደ ተራራው በወጣሁ ጊዜ፣ እህል ሳልበላ፣ ውሃም ሳልጠጣ አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ቈየሁ፤

10. በእግዚአብሔር (ያህዌ) ጣት የተጻፈባቸውን ሁለት የድንጋይ ጽላቶች እግዚአብሔር (ያህዌ) ሰጠኝ፤ በተሰበሰባችሁበት ዕለት እግዚአብሔር (ያህዌ) ከተራራው ላይ በእሳት ውስጥ ሆኖ ለእናንተ የነገራችሁ ትእዛዛት ሁሉ በእነርሱ ላይ ነበሩባቸው።

11. አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ከተፈጸመ በኋላ፣ እግዚአብሔር (ያህዌ) ሁለቱን የድንጋይ ጽላቶች ማለትም የኪዳኑን ጽላቶች ሰጠኝ።

12. ከዚያም እግዚአብሔር (ያህዌ)፣ “ተነሣ፤ ከግብፅ ያወጣሃቸው ሕዝብህ ረክሰዋልና ፈጥነህ ከዚህ ውረድ፤ እኔ ካዘዝኋቸው ፈጥነው ፈቀቅ ብለዋል፤ ቀልጦ የተሠራ ጣዖትም ለራሳቸው አበጅተዋል” ብሎ ነገረኝ።

13. ደግሞም እግዚአብሔር (ያህዌ) እንዲህ አለኝ፤ “ይህን ሕዝብ አይቼዋለሁ፤ በእርግጥ ዐንገተ ደንዳና ሕዝብ ነው፣

14. አጠፋቸውና ስማቸውንም ከሰማይ በታች እደመስሰው ዘንድ ተወኝ፤ አንተንም ከእነርሱ ይልቅ ብርቱና ብዙ ሕዝብ አደርግሃለሁ።”

15. ስለዚህ ተራራው በእሳት እየተቀጣጠለ ሳለ፣ ሁለቱን የቃል ኪዳን ጽላቶች በሁለቱም እጆቼ እንደያዝሁ ከተራራው ተመልሼ ወረድሁ።

16. በእርግጥ በአምላካችሁ በእግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) ላይ ኀጢአት ሠርታችሁ እንደ ነበር ተመለከትሁ፤ ቀልጦ የተሠራ የጥጃ ምስልም ለራሳችሁ አበጃችሁ፤ እግዚአብሔር (ያህዌ) እናንተን ካዘዛችሁ መንገድ በፍጥነት ወጥታችሁ ነበር።

17. ስለዚህ ሁለቱን ጽላቶች ወስጄ ከእጆቼ አሽቀንጥሬ በፊታችሁ ሰባ በርኋቸው።

18. ከዚያም በእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት ክፉ ነገርን በመፈጸም ለቊጣ እንዲነሣሣ የሚያደርገውን ኀጢአት ሁሉ ስለ ሠራችሁ፣ እህል ውሃ ሳልቀምስ አርባ ቀንና አርባ ሌሊት እንደ ገና በእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት በግምባሬ ተደፋሁ።

19. እናንተን ሊያጠፋችሁ ክፉኛ ተቈጥቶ ነበርና፣ እኔም የእግዚአብሔርን (ያህዌ) ቊጣና መዓት ፈራሁ፤ እግዚአብሔር (ያህዌ) ግን እንደ ገና ሰማኝ።

20. እግዚአብሔር (ያህዌ) አሮንን ሊያጠፋው ክፉኛ ተቈጥቶ ነበር፤ በዚያን ጊዜ ለአሮንም ጸለይሁ።

21. ደግሞም ያን የኀጢአት ሥራችሁን፣ አበጅታችሁት የነበረውን ጥጃ ወስጄ፣ በእሳት አቃጠልሁት፤ ከዚያም ሰባብሬ እንደ ትቢያ ዱቄት እስኪሆን ድረስ ፈጭቼ ከተራራው በሚወርደው ጅረት ውስጥ በተንሁት።

22. በተቤራም፣ በማሳህና በቂብሮት ሐታአዋ እግዚአብሔርን (ያህዌ) አስቈጣችሁት።

23. እግዚአብሔር (ያህዌ) ከቃዴስ በርኔ ባስ ወጣችሁ ጊዜ፣ “ውጡ፤ የሰጠኋችሁንም ምድር ርስት አድርጋችሁ ውረሷት” አላችሁ። እናንተ ግን በአምላካችሁ በእግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) ትእዛዝ ላይ ዐመፃችሁ፤ እርሱን አልታመናችሁበትም፤ አልታዘዛችሁትምም።

24. እኔ እናንተን ካወቅኋችሁ ጊዜ ጀምሮ፣ በእግዚአብሔር (ያህዌ) ላይ እንዳመፃችሁ ናችሁ።

25. እግዚአብሔር (ያህዌ) እናንተን እንደሚያ ጠፋችሁ ተናግሮ ስለ ነበር፣ በእነዚያ አርባ ቀናትና አርባ ሌሊቶች በእግዚአብሔር ፊት በግንባሬ ተደፋሁ፤

26. እንዲህም በማለት ወደ እግዚአብሔር (ያህዌ) ጸለይሁ፤ “ጌታ እግዚአብሔር ሆይ (አዶናይ ያህዌ) በታላቅ ኀይልህ የተቤዠኸውንና በኀያል ክንድህ ከግብፅ ያወጣኸውን፣ ያንተ ርስት የሆነውን ሕዝብህን አታጥፋ።

27. ባሪያዎችህን አብርሃምን፣ ይስሐቅንና ያዕቆብን አስብ፤ የዚህን ሕዝብ ልበ ደንዳናነት፣ ክፋትና ኀጢአት አትመልከት።

28. አለበለዚያ እኛን ካመጣህበት ምድር ያሉ ሰዎች “እግዚአብሔር (ያህዌ) ተስፋ ወደ ሰጣቸው ምድር ሊያገባቸው ስላልቻለና ስለጠላቸው፤ ‘በምድረ በዳ ሊገድላቸው አወጣቸው ይላሉ።’

29. ነገር ግን እነርሱ በታላቅ ኀይልህና በተዘረጋች ክንድህ ያወጣሃቸው ሕዝብህና ርስትህ ናቸው።”