ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12
  13. 13
  14. 14
  15. 15
  16. 16
  17. 17
  18. 18
  19. 19
  20. 20
  21. 21
  22. 22
  23. 23
  24. 24
  25. 25
  26. 26
  27. 27
  28. 28
  29. 29
  30. 30
  31. 31
  32. 32
  33. 33
  34. 34

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘዳግም 22 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. የወንድምህ በሬ ወይም በግ ጠፍቶ ሲባዝን ብታየው፣ ወደ እርሱ መልሰህ አምጣለት እንጂ ዝም ብለህ አትለፈው፤

2. ወንድምህ በአቅራቢያህ ባይኖር፣ ወይም የማን መሆኑን የማታውቅ ከሆነ፣ ባለቤቱ ፈልጎት እስኪመጣ ድረስ፣ ወደ ቤትህ ወስደህ ከአንተ ዘንድ አቈየው፤ ከዚያም መልሰህ ስጠው።

3. የወንድምህን አህያ ወይም ልብስ ወይም የጠፋበትን ማናቸውንም ነገር ስታገኝ እንደዚሁ አድርግ፤ በቸልታ አትለፈው።

4. የወንድምህ አህያ ወይም በሬ መንገድ ላይ ወድቆ ብታየው፣ በእግሩ እንዲቆምለት ርዳው እንጂ ዐልፈኸው አትሂድ።

5. ሴት የወንድ ልብስ አትልበስ፤ ወንድም የሴት ልብስ አይልበስ፤ እንዲህ የሚያደርገውን ሁሉ አምላክህእግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) ይጸየፈዋልና።

6. በመንገድ ስታልፍ፣ አንዲት ወፍ ጫጩቶቿን ወይም ዕንቁላሎቿን የታቀፈችበትን ጐጆ በዛፍ ወይም በመሬት ላይ ብታገኝ፣ እናቲቱን ከነጫጩቶቿ አትውሰድ፤

7. ጫጩቶቿን መውሰድ ትችላለህ፤ እናቲቱን ግን መልካም እንዲሆንልህና ዕድሜህም እንዲረዝም ልቀቃት፤

8. አዲስ ቤት በምትሠራበት ጊዜ፣ ከጣራው ላይ ሰው ወድቆ በቤትህ ላይ የደም በደል እንዳታመጣ፣ በጣራው ዙሪያ መከታ አብጅለት።

9. በወይን ተክል ቦታህ ውስጥ ሁለት ዐይነት ዘር አትዝራ፤ ይህን ካደረግህ፣ የዘራኸው ሰብል ብቻ ሳይሆን፣ የወይን ፍሬህም ይጠፋል።

10. በሬና አህያ በአንድ ላይ ጠምደህ አትረስ።

11. ሱፍና በፍታ አንድ ላይ ተፈትሎ የተሠራ ልብስ አትልበስ።

12. በምትለብሰው ልብስ ላይ በአራቱ ማእዘኖች ዘርፍ አድርግ።

ጋብቻን በንጽሕና ስለ መጠበቅ

13. አንድ ወንድ ሚስት አግብቶ አብሮአት ከተኛ በኋላ ቢጠላት፣

14. ስሟንም በማጥፋት፣ “ይህችን ሴት አገባኋት፤ ዳሩ ግን በደረስሁባት ጊዜ ድንግልናዋን አላገኘሁም” ቢል፣

15. የልጂቱ አባትና እናት ድንግልናዋን የሚያረጋግጥ ማስረጃ ይዘው በከተማዪቱ በር ወዳሉት አለቆች ይምጡ።

16. የልጂቱም አባት ለአለቆቹ እንዲህ ይበል፤ “ልጄን ለዚህ ሰው ዳርሁለት፤ እርሱ ግን ጠላት፤

17. ስሟንም በማጥፋት፣ ‘ልጅህን ከነድንግልናዋ አላገኘኋትም’ ብሎኛል፤ ነገር ግን የልጄ ድንግልና ማረጋገጫ ይኸውላችሁ፤” ከዚያም ወላጆቿ የደሙን ሸማ በከተማዪቱ አለቆች ፊት ይዘርጉት።

18. ከዚያም በኋላ አለቆቹ ሰውየውን ይዘው ይቅጡት፤

19. ይህ ሰው የአንዲት እስራኤላዊት ድንግል ስም አጥፍቶአልና አንድ መቶ ሰቅል ብር ያስከፍሉት፤ ገንዘቡንም ለልጂቱ አባት ይስጡት፤ ሴቲቱም ሚስቱ ሆና ትኖራለች፤ በሕይወት ዘመኑ ሁሉ ሊፈታት አይችልም።

20. ሆኖም ክሱ እውነት ሆኖ ሴቲቱ ድንግል ለመሆኗ ምንም ማረጋገጫ ማቅረብ ካልተቻለ፣

21. ገና በአባቷ ቤት ሳለች በማመንዘር በእስራኤል ውስጥ ወራዳ ተግባር ፈጽማለችና ወደ አባቷ ቤት ደጃፍ ያምጧት፤ እዚያም የከተማዋ ሰዎች እስክትሞት ድረስ በድንጋይ ይውገሯት። ክፉውን ከመካከልህ ማስወገድ አለብህ።

22. አንድ ሰው፣ ከሌላ ሰው ሚስት ጋር ተኝቶ ቢገኝ፣ አብሮአት የተኛው ሰውና ሴቲቱ ሁለቱም ይገደሉ፤ ክፉውን ከእስራኤል ማስወገድ አለብህ።

23. አንድ ሰው የታጨች ድንግል በከተማ ውስጥ አግኝቶ ከእርሷ ጋር ቢተኛ፣

24. ልጃገረዲቱ በከተማ ውስጥ እያለች አስጥሉኝ ብላ ስላልጮኸች፣ ሰውየውም የሌላን ሰው ሚስት አስገድዶ ስለደፈረ፣ ሁለቱንም ወደ ከተማ ደጃፍ ወስዳችሁ እስኪሞቱ ድረስ በድንጋይ ውገሯቸው። ክፉውን ከመካከልህ ማስወገድ አለብህ።

25. ነገር ግን አንድ ሰው የታጨችውን ልጃገረድ ከከተማ ውጭ አግኝቶ በማስገደድ ቢደፍራት፣ ይህን ድርጊት የፈጸመው ሰው፣ ብቻ ይገደል።

26. በልጃገረዲቱ ላይ ግን ምንም አታድርጉባት፤ ለሞት የሚያበቃ ኀጢአት ምንም አልሠራችም፤ ይህ ዐይነቱ ጒዳይ፣ አደጋ ጥሎ ባልንጀራውን ከሚገድል ሰው አድራጎት ጋር የሚመሳሰል ነው።

27. ምክንያቱም ሰውየው የታጨችውን ልጃገረድ ከከተማ ውጭ ስላገኛትና ብትጮኽም እንኳ ለርዳታ የደረሰላት ማንም ሰው ስላልነበር ነው።

28. አንድ ሰው ያልታጨች ልጃገረድ አግኝቶ በማስገደድ ቢደርስባትና ቢጋለጡ፣

29. ሰውየው ለልጅቷ አባት አምሳ ስቅል ብር ይክፈል፤ ልጃገረዲቱን አስገድዶ ደፍሮአታልና እርሷን ማግባት አለበት፤ በሕይወት ዘመኑ ሁሉ ሊፈታት አይችልም።

30. አንድ ሰው የአባቱን ሚስት ማግባት የለበትም፤ የአባቱንም መኝታ አያርክስ።