ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘዳግም 20:5-20 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

5. አለቆቹም ለሰራዊቱ እንዲህ ይበሉ፤ “አዲስ ቤት ሠርቶ ያላስመረቀ አለን? ወደ ቤቱ ተመልሶ ይሂድ፤ ያለበለዚያ በጦርነቱ ላይ ይሞትና ቤቱን የሚያስመርቀው ሌላ ሰው ይሆናል።

6. ወይን ተክሎ ገና ያልበላለት አለን? ወደ ቤቱ ይመለስ፤ ያለበለዚያ በጦርነቱ ላይ ይሞትና ወይኑን ሌላ ሰው ይበላዋል።

7. ሚስት አጭቶ ያላገባት አለን? ወደ ቤቱ ይመለስ፤ ያለበለዚያ በጦርነቱ ይሞትና ሌላ ሰው ያገባታል።”

8. ከዚያም አለቆቹ፣ “የሚፈራ ወይም ልቡ የሚባባ ሰው አለን? የወንድሞቹም ልብ እንዳይባባ ወደ ቤቱ ይመለስ” በማለት ጨምረው ይናገሩ።

9. አለቆቹ ለሰራዊቱ ተናግረው ሲያበቁ፣ አዛዦችን በሰራዊቱ ላይ ይሹሙ።

10. አንድን ከተማ ለመውጋት በምትዘምትበት ጊዜ፣ አስቀድመህ ለሕዝቧ የሰላም ጥሪ አስተላልፍ፤

11. ከተቀበሉህና ደጃቸውን ከከፈቱልህ በከተማዋ ውስጥ ሕዝብ ሁሉ ገባርህ ይሁን፤ ያገልግልህም።

12. ዕርቀ ሰላምን ባለመቀበል ውጊያን ከመረጡ፤ ከተማዪቱን ክበባት።

13. አምላክህ እግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) አሳልፎ በእጅህ በሰጠህ ጊዜ፣ በውስጧ ያሉትን ወንዶች በሙሉ በሰይፍ ግደላቸው።

14. ነገር ግን ሴቶቹን ሕፃናትን፣ እንስሳቱንና በከተማዪቱ ውስጥ የሚገኘውን ማናቸውንም ነገር በምርኮ ለራስህ አድርግ አምላክህ እግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) ከጠላቶችህ የሚሰጥህን ምርኮ ልትጠቀምበት ትችላለህ።

15. እንግዲህ የአካባቢህ አሕዛብ ከተሞች ባልሆኑትና ከአንተ እጅግ ርቀው በሚገኙት ከተሞች ሁሉ ላይ የምታደርገው ይኸው ነው።

16. አምላክህ እግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) ርስት አድርጎ በሚሰጥህ በአሕዛብ ከተሞች ውስጥ፣ እስትንፋስ ያለውን ነገር አታስተርፍ፤

17. ኬጢያዊውን፣ አሞራዊውን፣ ከነዓናዊውን፣ ፌርዛዊውን፣ ኤዊያዊውን፣ ኢያቡሳዊውን አምላክህ እግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) ባዘዘህ መሠረት ፈጽመህ ደምስሳቸው፤

18. አለበለዚያ አማልክታቸውን በሚያመልኩበት ጊዜ የሚፈጽሟቸውን አስጸያፊ ተግባራት ሁሉ ታደርግ ዘንድ ያስተምሩሃል፤ በአምላክህበእግዚአብሔርም (ኤሎሂም ያህዌ) ላይ ኀጢአት ትሠራለህ።

19. አንድን ከተማ ተዋግተህ ለመያዝ የረጅም ጊዜ ከበባ ካደረግህ፣ ዛፎቹን በመጥረቢያ ጨፍጭፈህ አታጥፋ፤ የእነርሱን ፍሬ መብላት ትችላለህና አትቊረጣቸው፤ ከበህ የምታጠፋቸው የሜዳ ዛፎች ሰዎች ናቸውን?

20. የሚበላ ፍሬ እንደማያፈራ የምታውቀውን ዛፍ ግን ልትቈርጠውና ጦርነት የምታካሄድባትን ከተማ በድል እስክትቈጣጠራት ድረስ ለከበባው ምሽግ መሥሪያ ልትጠቀምበት ትችላለህ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘዳግም 20