ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12
  13. 13
  14. 14
  15. 15
  16. 16
  17. 17
  18. 18
  19. 19
  20. 20
  21. 21
  22. 22
  23. 23
  24. 24
  25. 25
  26. 26
  27. 27
  28. 28
  29. 29
  30. 30
  31. 31
  32. 32
  33. 33
  34. 34

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘዳግም 17 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. እንከን ወይም ጒድለት ያለበትን በሬ ወይም በግ በእርሱ ዘንድ አስጸያፊ ነውና ለአምላክህለእግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) አትሠዋ።

2. እግዚአብሔር (ያህዌ) በሚሰጥህ ከተሞች በአንዲቱ አብሮህ የሚኖር ወንድ ወይም ሴት ኪዳኑን በማፍረስ በአምላክህ በእግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) ፊት ክፉ ድርጊት ሲፈጽም ቢገኝ፣

3. ትእዛዜንም በመተላለፍ ባዕዳን አማልክትን ያመለከ፣ ለእርሱም ማለትም ለፀሓይ ወይም ለጨረቃ ወይም ለሰማይ ከዋክብት የሰገደ፣

4. አንተም ይህ መደረጉን ብትሰማ፣ ነገሩን በጥንቃቄ መርምር፤ የተባለውም እውነት ከሆነና እንዲህ ያለው አስጸያፊ ነገር በእስራኤል ዘንድ መፈጸሙ ከተረጋገጠ፣

5. ይህን ክፉ ድርጊት የፈጸመውን ወንድ ወይም ሴት ወደ ከተማ ደጅ ወስደህ፣ ያን ሰው እስኪሞት ድረስ በድንጋይ ውገረው።

6. ሞት የሚገባው ሰው፣ በሁለት ወይም በሦስት ሰዎች ምስክርነት ይገደል፤ ነገር ግን በአንድ ሰው ምስክርነት ብቻ ማንም ሰው አይገደል።

7. ሲገደልም መጀመሪያ የምስክሮቹ እጅ፣ ቀጥሎም የሕዝቡ ሁሉ እጅ ይረፍበት፤ ክፉን ከመካከልህ አስወግድ።

የፍርድ አደባባይ

8. በአንድ የነፍስ ግድያ ዐይነትና በሌላ፣ በአንድ ዐይነት ሕጋዊ ክርክርና በሌላ፣ ወይም በአንድ የክስ ዐይነትና በሌላ መካከል ውሳኔ የሚጠይቅ ማንኛውም ጒዳይ ቢነሣ፣ ከዐቅምህ በላይ የሆነ ጒዳይ በከተሞችህ ውስጥ ቢያጋጥምህ፣ ተነሥተህ አምላክህ እግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) ወደሚመርጠው ስፍራ ውጣ፤

9. ካህናት ወደሆኑት ሌዋውያንና በዚያን ጊዜ ዳኛ ወደ ሆነው ሰው ሄደህ፣ ስለ ጒዳዩ ጠይቃቸው፤ እነርሱም ውሳኔውን ይነግሩሃል።

10. አንተም እግዚአብሔር (ያህዌ) በሚመርጠው ስፍራ እነርሱ በሚሰጡህ ውሳኔ መሠረት ፈጽም፤ እንድ ትፈጽም የሚሰጡህን መመሪያ ሁሉ በጥንቃቄ አድርግ።

11. በሚያስተምሩህ ሕግና በሚሰጡህ መመሪያዎች መሠረት ፈጽም። እነርሱ ከሚነግሩህ ቀኝም ግራም አትበል።

12. አምላክህን እግዚአብሔርን (ኤሎሂም ያህዌ) ለማገልገል በዚያ የሚቆመውን ካህን ወይም ዳኛ የሚንቅ ይገደል፤ ከእስራኤልም መካከል ክፉውን አስወግድ።

13. ሕዝቡም ሁሉ ይህን ሲሰማ ይፈራል፤ ከዚያ ወዲያም እንዲህ ያለውን የንቀት ድርጊት አይደግመውም።

ንጉሥን ስለማንገሥ

14. አምላክህ እግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) ወደሚሰጥህ ምድር ስትገባ፣ በምትወርሳትና በምትቀመጥባት ምድር፣ “በዙሪያዬ እንዳሉት አሕዛብ ሁሉ፣ እኔም በላዬ ንጉሥ ላንግሥ” ብትል፣

15. አምላክህ እግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) የሚመርጠውን ንጉሥ በላይህ ታነግሣለህ፤ ከገዛ ወንድሞችህ መካከል እንጂ፣ እስራኤላዊ ወንድምህ ያልሆነውን ባዕድ በላይህ አታንግሥ።

16. ንጉሡም ብዙ ፈረሶችን ለራሱ አያብዛ፤ ወይም ደግሞ የፈረሰኞችን ቊጥር ለመጨመር ሕዝቡን ወደ ግብፅ አይመልስ፤ እግዚአብሔር (ያህዌ)፣ “በዚያ መንገድ ፈጽሞ አትመለሱ” ብሎአችኋልና።

17. ልቡ እንዳይስትም ብዙ ሚስቶችን አያግባ፤ ብዙ ብርና ወርቅም አያግበስብስ።

18. በመንግሥቱ ዙፋን ላይ በሚቀመጥበትም ጊዜ የዚህን ሕግ ቅጅ ከሌዋውያን ካህናት ወስዶ በጥቅልል መጽሐፍ ለራሱ ይጻፍ።

19. አምላኩን እግዚአብሔርን (ኤሎሂም ያህዌ) ማክበር ይማር ዘንድ፣ የዚህን ሕግ ቃል ሁሉና ይህን ሥርዐት በጥንቃቄ ይከተል ዘንድ ከእርሱ ጋር ይሁን፤ በሕይወቱ ዘመን ሁሉ ያንብበው፤

20. እርሱና ዘሮቹ በእስራኤል ላይ ረጅም ዘመን ይገዙ ዘንድ፣ ከሕጉ ቀኝም ግራም አይበል፤ ራሱን ከሌሎች ወንድሞቹ በላይ የተሻለ አድርጎ አይቊጠር።