ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘካርያስ 12:1-8 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. ስለ እስራኤል የተነገረው የእግዚአብሔር ቃል ይህ ነው፤ ሰማያትን የዘረጋ፣ ምድርን የመሠረተ የሰውንም መንፈስ በውስጡ የሠራ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤

2. “ኢየሩሳሌምን በዙሪያዋ ላሉት ሕዝቦች ሁሉ የሚያንገደግድ ጽዋ አደርጋታለሁ፤ ይሁዳም እንደ ኢየሩሳሌም ሁሉ ትከበባለች።

3. የምድር አሕዛብ ሁሉ በእርሷ ላይ በሚሰበሰቡበት በዚያ ቀን፣ ኢየሩሳሌምን ለአሕዛብ ሁሉ የማይነቃነቅ ዐለት አደርጋታለሁ፤ ለማነቃነቅ የሚሞክሩ ሁሉ ራሳቸውን ይጐዳሉ።

4. በዚያን ቀን እያንዳንዱን ፈረስ በድንጋጤ፣ የተቀመጡባቸውንም ሰዎች እብደት እመታለሁ” ይላል እግዚአብሔር። “የይሁዳን ቤት በዐይኔ እጠብቃለሁ፤ ነገር ግን የአሕዛብን ፈረሶች ሁሉ አሳውራለሁ።

5. የይሁዳ መሪዎች በልባቸው፣ ‘የኢየሩሳሌም ሕዝቦች ብርቱ ናቸው፤ አምላካቸው እግዚአብሔር ጸባኦት ነውና’ ይላሉ።

6. “በዚያ ቀን የይሁዳን መሪዎች በዕንጨት ክምር ውስጥ እንዳለ የእሳት ምድጃ፣ በነዶም መካከል እንዳለ የፋና ነበልባል አደርጋቸዋለሁ፤ በግራና በቀኝ ዙሪያውን ያሉትን ሕዝቦች ይበላሉ፤ ኢየሩሳሌም ግን ከስፍራዋ ንቅንቅ አትልም።

7. “የዳዊት ቤትና የኢየሩሳሌም ነዋሪዎች ክብር ከይሁዳ ክብር እንዳይበልጥ እግዚአብሔር በመጀመሪያ የይሁዳን መኖሪያዎች ያድናል።

8. ከመካከላቸው እጅግ ደካማ የሆነው እንደ ዳዊት፣ የዳዊት ቤትምፊት ፊታቸው እንደሚሄድ እንደ እግዚአብሔር መልአክ፣ እንደ አምላክ ይሆንላቸው ዘንድ በኢየሩሳሌም የሚኖሩትን እግዚአብሔር ይከልላቸዋል።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘካርያስ 12