ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘኁልቍ 31:16-30 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

16. የበለዓምን ምክር ተቀብለው በፌጎር በተፈጸመው ድርጊት እስራኤላውያን ከእግዚአብሔር (ያህዌ) እንዲመለሱና የእግዚአብሔርም (ያህዌ) ሕዝብ እንዲቀሠፍ ያደረጉት እነርሱ ናቸው።

17. አሁንም ወንዶቹን ልጆች ሁሉ፣ ወንድ ያወቊትንም ሴቶች በሙሉ ግደሉዋቸው፤

18. ነገር ግን ወንድ ያላወቁትን ልጃገረዶች ሁሉ ለራሳችሁ አስቀሩአቸው።

19. “ከእናንት መካከል ሰው የገደለ ወይም የተገደለውን የነካ ሁሉ ከሰፈር ውጭ ሰባት ቀን ይቈይ። በሦስተኛውና በሰባተኛው ቀን ራሳችሁንና ምርኮኞቻችሁን አንጹ።

20. ማናቸውንም ልብስ እንዲሁም ከቈዳ፣ ከፍየል ጠጒር ወይም ከዕንጨት የተሠራ ማንኛውንም ነገር አንጹ።”

21. ከዚያም ካህኑ አልዓዛር ወደ ጦርነት ሄደው የነበሩትን ወታደሮች እንዲህ አላቸው፤ “እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሙሴ የሰጠው የሕጉ ሥርዐት ይህ ነው፤

22. ወርቅ፣ ብር፣ ናስ፣ ብረት፣ ቈርቈሮ፣ እርሳስ

23. እንዲሁም እሳትን መቋቋም የሚችል ማንኛውም ነገር በእሳት ውስጥ ማለፍ አለበት፤ ከዚያም ንጹሕ ይሆናል፤ ይህም ሆኖ መንጻት አለበት። እሳትን መቋቋም የማይችል ማንኛውም ነገር በዚሁ ውሃ ውስጥ ማለፍ አለበት።

24. በሰባተኛው ቀን ልብሳችሁን እጠቡ፤ ትነጻላችሁም፤ ከዚያም ወደ ሰፈር መግባት ትችላላችሁ።”

25. እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን እንዲህ አለው፤

26. “አንተ፣ ካህኑ አልዓዛርና በማኅበረ ሰቡ ውስጥ ያሉት የየቤተ ሰቡ አለቆች ሆናችሁ የተማረከውን ሕዝብና እንስሳት ሁሉ ቊጠሩ።

27. ምርኮውንም ለሁለት ከፍላችሁ በጦርነቱ ለተካፈሉት ወታደሮችና ለቀረው ማኅበረሰብ አከፋፍሉት።

28. በጦርነቱ ከተካፈሉት ወታደሮች ድርሻ ላይ፣ ከሰውም ሆነ ከቀንድ ከብት፣ ከአህያ፣ ከበግ ወይም ከፍየል ከየአምስት መቶው አንዱን ለእግዚአብሔር (ያህዌ) ግብር አውጣ።

29. ይህንንም ግብር ከድርሻቸው ላይ ወስደህ የእግዚአብሔር (ያህዌ) ፈንታ በማድረግ ለካህኑ ለአልዓዛር ስጠው።

30. ከእስራኤላውያን እኩሌታ ድርሻ ደግሞ ከሰውም ይሁን ከቀንድ ከብት፣ ከአህያ፣ ከበግ፣ ከፍየል ወይም ከሌሎች እንስሳት ከየአምሳው አንዳንድ መርጠህ፣ የእግዚአብሔርን (ያህዌ) ማደሪያ ድንኳን በኀላፊነት ለሚጠብቁ ሌዋውያን ስጣቸው።”

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘኁልቍ 31