ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘኁልቍ 23:3-18 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

3. ከዚያም በለዓም ባላቅን፣ “እኔ ወደዚያ ስሄድ፣ አንተ እዚሁ መሥዋዕትህ አጠገብ ቈይ፤ ምናልባትም እግዚአብሔር (ያህዌ) ሊገናኘኝ ይመጣ ይሆናል፤ የሚገልጥልኝንም ሁሉ እነግርሃለሁ” አለው። ከዚያም በለዓም ወደ አንድ ገላጣ ኰረብታ ሄደ።

4. እግዚአብሔር (ኤሎሂም) ተገናኘው፤ በለዓምም፣ “እነሆ፤ ሰባት መሠዊያዎች አዘጋጅቻለሁ፤ በእያንዳንዱም ላይ አንድ ኮርማና አንድ አውራ በግ አቅርቤአለሁ” አለው።

5. እግዚአብሔርም (ያህዌ) በበለዓም አፍ መልእክት አስቀምጦ፣ “ወደ ባላቅ ተመልሰህ ይህን መልእክት ንገረው” አለው።

6. እርሱም ተመልሶ ሲሄድ ባላቅን ከመላው የሞዓብ አለቆች ጋር በመሠዊያው አጠገብ ቆሞ አገኘው።

7. ከዚያም በለዓም ንግሩን እንዲህ ሲል ጀመረ፤“ባላቅ ከአራም አመጣኝ፣የሞዓብ ንጉሥ ከምሥራቅ ተራሮች።‘ና ያዕቆብን ርገምልኝ፤መጥተህም እስራኤልን አውግዝልኝ’ አለኝ።

8. እግዚአብሔር (ኤሎሂም) ያልረገመውን፣እኔ እንዴት ረግማለሁ? እግዚአብሔር (ያህዌ) ያላወገዘውንስ፣እንዴት አወግዛለሁ?

9. ከዐለታማ ተራሮች ጫፍ ሆኜ አየዋለሁ፤በከፍታዎቹም ላይ ሆኜ እመለከተዋለሁ፤ተለይቶ የሚኖረውን፣ራሱንም ከሌሎች ሕዝቦች ጋር የማይቈጥረውን፣ ሕዝብ አያለሁ።

10. የያዕቆብን ትቢያ ማን ቈጥሮ ይዘልቃል?የእስራኤልንስ ሩብ ማን ይቈጥረዋል።የጻድቁን ሞት እኔ ልሙት፤ፍጻሜዬም የእርሱ ዐይነት ፍጻሜ ትሁን!”

11. ባላቅም በለዓምን፣ “እንዴት እንዲህ ታደርገኛለህ? ጠላቶቼን እንድትረግምልኝ አመጣሁህ፤ አንተ ግን ባረክሃቸው እንጂ ምንም አላደረግህልኝም!” አለው።

12. እርሱም መልሶ “እግዚአብሔር (ያህዌ) በአፌ ያስቀመጠውን መናገር አይገባኝምን?” አለው።

13. ከዚህ በኋላ ባላቅ፣ “እነርሱን ማየት ወደ ምትችልበት ወደ ሌላ ቦታ እንሂድ፤ እዚያም ሁሉን ሳይሆን በከፊል ብቻ ታያቸዋለህ፤ እዚያም ሆነህ እነርሱን ርገምልኝ” አለው።

14. ስለዚህም በፈስጋ ተራራ ጫፍ ላይ ወዳለው ወደ ጾፊም ሜዳ ወሰደው፤ እዚያም ሰባት መሠዊያ ሠርቶ በእያንዳንዱ ላይ አንድ ኮርማና አንድ አውራ በግ ሠዋ።

15. በለዓምም ባላቅን፣ “እርሱን ለመገናኘት ወደዚያ ስሄድ፣ አንተ እዚሁ መሥዋዕትህ አጠገብ ቈይ” አለው።

16. እግዚአብሔር (ያህዌ) በለዓምን ተገናኘው፤ በአፉም መልእክት አስቀምጦ፣ “ወደ ባላቅ ተመለስና ይህን መልእክት ንገረው” አለው።

17. እርሱም ተመልሶ ሲሄድ ባላቅን ከመላው የሞዓብ አለቆች ጋር በመሠዊያው አጠገብ ቆሞ አገኘው፤ ባላቅም፣ “እግዚአብሔር (ያህዌ) ምን አለ?” ሲል ጠየቀው።

18. ከዚያም ንግሩን እንዲህ ሲል ጀመረ፤“ባላቅ ሆይ ተነሣ፤ አድምጠኝ፤የሴፎር ልጅ ሆይ ስማኝ፤

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘኁልቍ 23