ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12
  13. 13
  14. 14
  15. 15
  16. 16
  17. 17
  18. 18
  19. 19
  20. 20
  21. 21
  22. 22
  23. 23
  24. 24
  25. 25
  26. 26
  27. 27

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘሌዋውያን 23 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን እንዲህ አለው፤

2. “ለእስራኤላውያን እንዲህ ብለህ ተናገር፤ ‘የተቀደሱ ጉባኤዎች ብላችሁ የምትዋጇቸው የተመረጡ የእግዚአብሔር (ያህዌ) በዓላት እነዚህ ናቸው፤

ሰንበት

3. “ ‘ሥራ የምትሠሩበት ስድስት ቀን አላችሁ፤ ሰባተኛው ቀን ግን የዕረፍት ሰንበት፣ የተቀደሰ ጉባኤ ዕለት ነው። የእግዚአብሔር (ያህዌ) ሰንበት ስለ ሆነ፣ በምትኖሩበት ስፍራ ሁሉ ምንም ዐይነት ሥራ አትሥሩበት።

የፋሲካና የቂጣ በዓል

4. “ ‘የተመረጡ የእግዚአብሔር (ያህዌ) በዓላት ብላችሁ በተወሰኑላቸው ጊዜያት የምታውጇቸው የተቀደሱ ጉባኤዎች እነዚህ ናቸው፤

5. የመጀመሪያው ወር በገባ በዐሥራ አራተኛው ቀን ምሽት የእግዚአብሔር (ያህዌ) ፋሲካ በዓል ይጀመራል።

6. በዚያው ወር በዐሥራ አምስተኛው ቀን የእግዚአብሔር (ያህዌ) የቂጣ በዓል ይጀመራል፤ ሰባት ቀንም ያለ እርሾ የተጋገረ ቂጣ ትበላላችሁ።

7. በመጀመሪያው ቀን የተቀደሰ ጉባኤ አድርጉ፤ የዕለት ተግባራችሁንም አታከናውኑ።

8. ሰባት ቀን በእሳት የሚቃጠል መሥዋዕት ለእግዚአብሔር (ያህዌ) አቅርቡ፤ በሰባተኛው ቀን የተቀደሰ ጉባኤ አድርጉ፤ በዚያ ዕለት የተለመደ ተግባራችሁን አታከናውኑ።’ ”

የበኵራት ስጦታ በዓል

9. እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን እንዲህ አለው፤

10. “ለእስራኤላውያን እንዲህ ብለህ ተናገር፤ ‘እኔ ወደምሰጣችሁ ምድር ገብታችሁ መከር በምትሰበስቡበት ጊዜ ከሰበሰባችሁት እህል የመጀመሪያውን ነዶ ለካህኑ አቅርቡ፤

11. ነዶው ተቀባይነት እንዲያገኝላችሁም በእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት ይወዝውዘው፤ ካህኑ ነዶውን የሚወዘውዘው በሰንበት ቀን ማግስት ነው።

12. ነዶውን በምትወዘውዙበት ቀን እንከን የሌለበትን የአንድ ዓመት ተባዕት የበግ ጠቦት የሚቃጠል መሥዋዕት እንዲሆን ለእግዚአብሔር (ያህዌ) አቅርቡ፤

13. ከዚህም ጋር ለእግዚአብሔር (ያህዌ) በእሳት የሚቀርብ፣ ሽታውም ደስ የሚያሰኝ እንዲሆን ሁለት ዐሥረኛ የኢፍ መስፈሪያ በዘይት የተለወሰ የላመ ዱቄት ለእህል ቊርባን፣ አንድ አራተኛ የኢን መስፈሪያ የወይን ጠጅ ለመጠጥ ቊርባን አቅርቡ።

14. ስጦታውን ለአምላካችሁ (ኤሎሂም) እስከምታቀርቡበት እስከዚያ ቀን ድረስ እንጀራም ቢሆን፣ ቈሎ ወይም እሸት አትብሉ፤ ይህም በምትኖሩበት ስፍራ ሁሉ ለሚመጡት ትውልዶች የዘላለም ሥርዐት ነው።

የመከር በዓል

15. “ ‘የሚወዘወዘውን የነዶ መሥዋዕት ካቀረባችሁበት የሰንበት ማግስት አንሥታችሁ ሰባት ሙሉ ሳምንታት ቊጠሩ።

16. እስከ ሰባተኛው ሰንበት ማግስት ድረስ አምሳ ቀን ቊጠሩ፤ ከዚያም የአዲስ እህል ቊርባን ለእግዚአብሔር (ያህዌ) አቅርቡ።

17. በሁለት ዐሥረኛ የኢፍ መስፈሪያ የላመ ዱቄት፣ በእርሾ የተጋገረ ሁለት እንጀራ ለሚወዘወዝ መሥዋዕት፣ የበኵራት ስጦታ እንዲሆን ከየቤታችሁ ለእግዚአብሔር (ያህዌ) አምጡ።

18. ከእንጀራውም ጋር ሰባት ነውር የሌለባቸው የአንድ ዓመት ተባዕት የበግ ጠቦቶች፣ አንድ ወይፈንና ሁለት አውራ በጎች አቅርቡ፤ እነዚህም ከእህል ቊርባናቸውና ከመጠጥ ቊርባናቸው ጋር ለእግዚአብሔር (ያህዌ) የሚቃጠል መሥዋዕት ይሆናሉ፤ ይህም በእሳት የሚቀርብ ሽታውም እግዚአብሔርን (ያህዌ) ደስ የሚያሰኝ መሥዋዕት ነው።

19. እንዲሁም አንድ ተባዕት ፍየል ለኀጢአት መሥዋዕት፣ ሁለት የአንድ ዓመት ተባዕት ጠቦቶችም ለኅብረት መሥዋዕት አቅርቡ።

20. ካህኑም ሁለቱን የበግ ጠቦቶች ከበኵራቱ እንጀራ ጋር የሚወዘወዝ መሥዋዕት አድርጎ በእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት ይወዘውዛቸዋል፤ እነዚህም ለእግዚአብሔር (ያህዌ) ቅዱስ መሥዋዕት፣ የካህኑም ድርሻ ናቸው።

21. በዚያኑ ዕለት የተቀደሰ ጉባኤ ዐውጁ፤ የተለመደ ተግባራችሁንም አታከናውኑ፤ ይህም በምትኖሩበት ስፍራ ሁሉ ለሚመጡት ትውልዶች የዘላለም ሥርዐት ነው።

22. “ ‘የምድራችሁን መከር በምትሰበስቡበት ጊዜ፣ የዕርሻችሁን ዳርና ዳር አትጨዱ፤ ቃርሚያውን አትልቀሙ፤ እነዚህንም ለድኾችና ለእንግዶች ተዉላቸው፤ እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ (ያህዌ ኤሎሂም) ነኝ።’

የመለከት በዓል

23. እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን እንዲህ አለው፤

24. “እስራኤላውያንን እንዲህ በላቸው፤ ‘የሰባተኛው ወር የመጀመሪያ ቀን ዕረፍት ይሁንላችሁ፤ በዚሁ በመለከት ድምፅ የሚከበር የተቀደሰ ጉባኤ ይኑራችሁ።

25. መሥዋዕትን በእሳት ለእግዚአብሔር (ያህዌ) አቅርቡ እንጂ የተለመደ ተግባራችሁን አታከናውኑበት።’ ”

የስርየት ቀን

26. እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን እንዲህ አለው፤

27. “የሰባተኛው ወር ዐሥረኛ ቀን የስርየት ቀን ነው፤ የተቀደሰ ጉባኤ አድርጉ፤ አንዳች ነገርም አትብሉ፤ መሥዋዕትም በእሳት ለእግዚአብሔር (ያህዌ) አቅርቡ።

28. በእግዚአብሔር (ያህዌ) በአምላካችሁ (ኤሎሂም) ፊት ለእናንተ ስርየት የሚደረግበት የስርየት ቀን ስለ ሆነ፣ በዚያ ዕለት ምንም ሥራ አትሥሩ።

29. በዚያ ዕለት ሰውነቱን የሚያጐሳቊል ማንኛውም ሰው ከወገኖቹ መካከል ተለይቶ ይጥፋ።

30. በዚያ ዕለት ማንኛውንም ሥራ የሚሠራውን ሰው ሁሉ ከወገኖቹ መካከል ለይቼ አጠፋዋለሁ።

31. ማንኛውንም ሥራ ከቶ አትሥሩበት፤ ይህ በምትኖሩበት ስፍራ ሁሉ ለልጅ ልጆቻችሁ የዘላለም ሥርዐት ነው።

32. ይህ ለእናንተ የዕረፍት ሰንበት ስለ ሆነ፣ ራሳችሁን ዝቅ ዝቅ አድርጉ በወሩም ከዘጠነኛው ቀን ምሽት ጀምራችሁ እስከሚቀጥለው ቀን ምሽት ድረስ ሰንበታችሁን አክብሩ።”

የዳስ በዓል

33. እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን እንዲህ አለው፤

34. “እስራኤላውያንን እንዲህ በላቸው፤ ‘ሰባተኛውም ወር በገባ በዐሥራ አምስተኛው ቀን የእግዚአብሔር (ያህዌ) የዳስ በዓል ይጀምራል፤ እስከ ሰባት ቀንም ይቆያል።

35. የመጀመሪያው ቀን የተቀደሰ ጉባኤ ነውና የተለመደ ተግባራችሁን አታከናውኑበት።

36. ሰባት ቀን መሥዋዕቱን በእሳት ለእግዚአብሔር (ያህዌ) አቅርቡ፤ በስምንተኛው ቀን የተቀደሰ ጉባኤ አድርጉ፤ መሥዋዕትን በእሳት ለእግዚአብሔር (ያህዌ) አቅርቡ፤ የተለመደ ተግባራችሁንም አታከናውኑበት።

37. “ ‘የሚቃጠል መሥዋዕትንና የእህል ቊርባንን፣ መሥዋዕትንና የመጠጥ ቊርባንን በተመደበላቸው ቀን ለእግዚአብሔር (ያህዌ) በእሳት ለማቅረብ፣ የተቀደሱ ጉባኤዎችን የምታውጁባቸው የእግዚአብሔር (ያህዌ) በዓላት እነዚህ ናቸው።

38. እነዚህ መሥዋዕቶች ለእግዚአብሔር (ያህዌ) ሰንበት ከምታቀርቡት፣ ከስጦታችሁ፣ ከስእለታችሁና ከበጎ ፈቃድ ስጦታችሁ በተጨማሪ የምታቀርቧቸው ስጦታዎች ናቸው።

39. “ ‘የምድራችሁን ፍሬ ከሰበሰባችሁ በኋላ በሰባተኛው ወር ከዐሥራ አምስተኛው ቀን ጀምራችሁ ሰባት ቀን ለእግዚአብሔር (ያህዌ) በዓል አክብሩ፤ የመጀመሪያው ቀን የዕረፍት ዕለት ነው፤ ስምንተኛውም ቀን እንደዚሁ የዕረፍት ዕለት ይሆናል።

40. በመጀመሪያው ቀን የመልካም ዛፍ ፍሬ፣ የዘንባባ ዝንጣፊ፣ የለመለመ ዛፍ ቅርንጫፍ የአኻያ ዛፍ ቅርንጫፍ ይዛችሁ ሰባት ቀን በአምላካችሁ በእግዚአብሔር (ኤሎሂም ያህዌ) ፊት ደስ ይበላችሁ።

41. በየዓመቱም የእግዚአብሔር (ያህዌ) በዓል አድርጋችሁ ሰባት ቀን አክብሩ፤ ይህም ለልጅ ልጃችሁ የዘላለም ሥርዐት ነው፤ በሰባተኛውም ወር አክብሩት።

42. ሰባት ቀን ዳስ ውስጥ ተቀመጡ፤ በትውልዱ እስራኤላዊ የሆነ ሁሉ ዳስ ውስጥ ይሰንብት፤

43. በዚህም እኔ እስራኤላውያንን ከግብፅ ባወጣሁ ጊዜ፣ ዳስ ውስጥ እንዲቀመጡ ማድረጌን የልጅ ልጆቻችሁ ያውቃሉ፤ እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ (ያህዌ ኤሎሂም) ነኝ።’ ”

44. በዚህ ሁኔታም ሙሴ የተመረጡትን የእግዚአብሔር (ያህዌ) በዓላት ለእስራኤላውያን አስታወቀ።