ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዘሌዋውያን 13:36-55 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

36. ካህኑ ይመርምረው፤ ቊስሉ በቈዳው ላይ ከሰፋ፣ ካህኑ የጠጒሩን ቢጫ መሆን አለመሆን ማየት አያሻውም፤ ሰውየው ርኩስ ነው።

37. ነገር ግን ቊስሉ በካህኑ አመለካከት ለውጥ ያላሳየ ከሆነና በውስጡ ጥቊር ጠጒር ካበቀለ ቊስሉ ድኖአል፤ ሰውየው ነጽቶአል፤ ካህኑም ንጹሕ መሆኑን ያስታውቅ።

38. “በወንድ ወይም በሴት ቈዳ ላይ ቋቍቻ ቢወጣ፣

39. ካህኑ ይመርምራቸው፤ ቋቍቻው ዳለቻ ከሆነ በቈዳ ላይ የወጣ ጒዳት የማያስከትል ችፍታ ነው፤ ሰውየውም ንጹሕ ነው።

40. “አንድ ሰው የራሱ ጠጒር ከዐናቱ አልቆ መላጣ ቢሆን ንጹሕ ነው።

41. ጠጒሩ ከፊት ለፊት ተመልጦ ራሰ በራ ቢሆንም ንጹሕ ነው።

42. ነገር ግን በመላጣው ወይም በበራው ላይ ነጣ ያለ ቀይ ቊስል ቢወጣበት፣ ያ ከመላጣው ወይም ከበራው የወጣ ተላላፊ በሽታ ነው።

43. ካህኑ ይመርምረው፤ በመላጣው ወይም በበራው ላይ ያበጠው ተላላፊ የቈዳ በሽታ የሚመስል ነጣ ያለ ቊስል ከሆነ፣

44. ሰውየው ደዌ አለበት፤ ርኵስም ነው፤ በራሱ ላይ ካለው ቊስል የተነሣም ሰውየው ርኩስ መሆኑን ካህኑ ያስታውቅ።

45. “እንዲህ ያለ ተላላፊ በሽታ ያለበት ሰው የተቀደደ ልብስ ይልበስ፤ ጠጒሩን ይግለጥ፤ እስከ አፍንጫውም ድረስ ተሸፋፍኖ ‘ርኩስ ነኝ ርኩስ ነኝ’ እያለ ይጩኽ።

46. ተላላፊ በሽታው እስካለበት ጊዜ ድረስ ርኩስ ነው፤ ብቻውን ይቀመጥ፤ ከሰፈር ውጪም ይኑር።

47. “ከበግ ጠጒር ወይም ከበፍታ የተሠራ ማንኛውም ዐይነት ልብስ በተላላፊ በሽታ ቢበከል፣

48. በሸማኔ ዕቃ ወይም በእጅ የተሠራ ማንኛውም ዐይነት የበግ ጠጒር ወይም የበፍታ ልብስ፣ ወይም ማንኛውም ቈዳ ወይም ከቈዳ የተሠራ ነገር ቢሆን፣

49. በልብስ ወይም በዐጐዛ፣ በሸማኔ ዕቃ በተሠራ ወይም በእጅ በተጠለፈ ወይም ከቈዳ በተሠራ ዕቃ ላይ አረንጓዴ ወይም ቀይ መሳይ ደዌ ቢከሠት፣ እየሰፋ የሚሄድ ተላላፊ በሽታ ስለ ሆነ ካህኑ ይየው።

50. ካህኑ ደዌውን ይመርምር፤ በደዌ የተበከለውንም ዕቃ ሰባት ቀን ያግልል።

51. በሰባተኛውም ቀን ይመርምረው፤ ደዌው በልብሱ፣ በሸማኔ ዕቃ በተሠራው ወይም በእጅ በተጠለፈው ጨርቅ ወይም ለማናቸውም አገልግሎት በሚውል ዐጐዛ ላይ ተስፋፍቶ ቢገኝ፣ ክፉ ደዌ ነው፤ ዕቃውም ርኩስ ነው።

52. ልብሱን ወይም በሸማኔ ዕቃ የተሠራውን ወይም በእጅ የተጠለፈውን የበግ ጠጒር ወይም በፍታ ወይም ደዌው ያለበትን ማንኛውንም ከቈዳ የተሠራ ዕቃ ያቃጥል፤ ደዌው ክፉ ነውና፤ ዕቃው ይቃጠል።

53. “ነገር ግን ካህኑ በሚመረምርበት ጊዜ ደዌው በልብሱ ወይም በሸማኔ ዕቃ በተሠራው ወይም በእጅ በተጠለፈው ጨርቅ ላይ፣ ወይም ከቈዳ በተሠራው ዕቃ ላይ ተስፋፍቶ ካልተገኘ፣

54. ካህኑ ደዌው ያለበት ነገር እንዲታጠብ ይዘዝ፤ ዕቃውንም ሰባት ቀን ደግሞ ያግልል።

55. ደዌው ያለበት ዕቃ ከታጠበ በኋላ ካህኑ ይመርምረው፤ ደዌው ባይስፋፋም እንኳ መልኩን ካልለወጠ፣ ርኩስ ነው፤ ደዌው የወጣው በውስጥም ሆነ በውጭ ዕቃው በእሳት ይቃጠል።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ዘሌዋውያን 13